በአፍሪካ ዋንጫ የምድብ ማጣሪያ የመጨረሻ ጨዋታ በምድብ 6 የሚገኙት ኬፕ ቬርድ እና ሊቢያ የሚያደርጉትን ጨዋታ እንዲዳኙ ኢትዮጵያዊን ዳኞች በካፍ ተመድበዋል፡፡
ኢንተርናሽናል አርቢቴር ባምላክ ተሰማ እና ረዳቶቹ ክንዴ ሙሴ እና ተመስገን ሳሙኤል ፕራያ ላይ ለሚደረገው ጨዋታ የተመረጡ ናቸው፡፡
ባምላክ ተሰማ እና ረዳቶቹ ነገ ዳሬ ሰላም ላይ ቅዳሜ ያንግ አፍሪካንስ እና ሞሊዲያ ኦሎምፒክ ቤጃያ የሚያደርጉትን የካፍ ኮንፌድሬሽን ካፕ የምድብ አንድ ጨዋታም ይዳኛሉ፡፡
ባምላክ እና ረዳቶቹ ከዚህ ቀደም በዚሁ ማጣሪያ ካሜሮን ከደቡብ አፍሪካ ያውንዴ ላይ ያደረጉትን ጨዋታ ማጫወታቸውን ይታወሳል፡፡ በቅርብ አመታት ውስጥ ካፍ ባምላክን ለአህጉራዊ የክለብ እና የሃገራት ጨዋታዎች በተደጋጋሚ መርጦታል፡፡
ከምድብ 6 ሞሮኮ አስቀድማ ወደ አፍሪካው ዋንጫው ያለፈች ሲሆን በሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጠችው ኬፕ ቬርድ በ9 ነጥብ ለጥሩ ሁለተኝነት ከሚፎካከሩት ሃገራት መካከል ትገኛለች፡፡ ሊቢያ ከአፍሪካ ዋንጫው ውጪ በመሆኗ ጨዋታውን የማሸነፍ ግዴታ ውስጥ የገባችው ኬፕ ቬርድ ናት፡፡