ማዳጋስካር ለምታስተናግደው የአፍሪካ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ለማለፍ ድሬዳዋ ላይ የግብፅ አቻውን ያስተናገደው የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን 2-1 በአጠቃላይ ውጤት 5-2 በማሸነፍ ወደ መጨረሻው የማጣሪያ ዙር ማለፍ ችሏል፡፡
በ11ኛው ደቂቃ አቡበከር ነስሮ ቀይ ቀበሮዎቹን ቀዳሚ ማድረግ ሲችል ግብፆች አቻ ለመሆን በመጀመሪያዎቹ ደቂቃዎች ጫና ፈጥረው ለመጫወት ሲሞክሩ ታይተዋል፡፡
በመጀመሪያው አጋማሽ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ኳስን ተቆጣጥሮ ለመጫወት ሲቸገር የታየ ሲሆን አማካይ እሱባለው ጌታቸው እና አቡበከር በግላቸውን የተሻለ ሲንቀሳቀሱ ታይተዋል፡፡
በ50ኛው ደቂቃ አቡበከር የግብፅ ተከላካዮች ስህተትን ተጠቅሞ መሪነቱን ወደ ሁለት አስፍቷል፡፡ አቡበከር በካይሮ ያስቆጠረውን ግብ ጨምሮ ግብጽ ላይ 3 ግቦች ማስቆጠር ችሏል፡፡
ሃዛማይ ፋርጋህል በ86ኛው ደቂቃ በቅጣት ምት የግብፅን ብቸኛ ግብ ማስቆጠር ችሏል፡፡ ለግቡ መቆጠር ግብ ጠባቂው ኦኛ ኡሞኛ ስህትት ነበረበት፡፡
ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድኑ ግብፅን ጥሎ ወደ ተከታዩ ዙር ማለፍ ችሏል፡፡ በቀጣዩ የማጣርያ ዙርም የአለም ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ የፍጻሜ ተፋላሚዋ ማሊን እንደምትገጥም ይጠበቃል፡፡ ማሊ ቻድን ከሜዳዋ ውጪ ኒጃሚና ላይ 9-0 ማሸነፍ ችላለች፡፡
በ1997 እ.ኤ.አ ቦትስዋና ተዘጋጅቶ በነበረው የአፍሪካ ታዳጊ ሻምፒዮና ኢትዮጵያ ለመጨረሻ ጊዜ የተሳተፈች ሲሆን በአሰልጣኝ ስዩም አባተ የሚመራው ቡድን አራተኛ ደረጃ ማጠናቀቁ የሚታወስ ነው፡፡