የኮፓ ኮካኮላ ከ15 አመት በታች የማጠቃለያ ውድድር በቢሾፍቱ ከተማ መካሄዱን ቀጥሏል፡፡ የሴቶች የምድብ ጨዋታዎችም ዛሬ በተደረጉ ጨዋታዎች ፍፃሜያቸውን አግኝተዋል፡፡
በምድብ ሀ ለምለም ተስፋ ት/ቤት ላይ በ3:00 ኦሮምያ ኢትዮ ሶማሌን ገጥሞ 1-0 በማሸነፍ በ100% ድል ምድቡን በበላይነት አጠናቋል፡፡ የኦሮምያን የድል ግብ የመጀመርያው አጋማሽ ሊጠናቀቅ 1 ደቂቃ ሲቀረው አጥቂዋ ቤተልሄም ስለሺ ከመረብ አሳርፋለች፡፡ በጨዋታው ኦሮምያዎች በርካታ የግብ እድሎች ፈጥረው የነበረ ቢሆንም ኮከብ ሆና የዋለችው የኢትዮ ሶማሌዋ ግብ ጠባቂ ገብሬሏ ተሾመን አልፈው ተጨማሪ ግብ ማስቆጠር አልቻሉም፡፡
በተመሳሳይ ሰአት ቢሾፍቱ ስታድየም ላይ ደቡብ አፋርን 3-0 በማሸነፍ ኦሮምያን ተከትሎ ግማሽ ፍፃሜውን ተቀላቅሏል፡፡ በረከት ፀጋዬ በ14ኛው ደቂቃ የመክፈቻውን ግብ ስታስቆጥር ዝናቧ አሰፋ በ55ኛው ፣ ብሩክ ወንድሙ በ79ኛው ደቂቃ ቀሪዎቹን ግቦች አስቆጥረዋል፡፡
የምድብ ሀ ሰንጠረዥ
1. ኦሮምያ 3 (+5) 9
2. ደቡብ 3 (+3) 6
– – – – – –
3. ኢትዮ ሶማሌ 3 (-4) 1
4. አፋር 3 (-5) 1
በምድብ ለ 05:00 ለምለም ተስፋ ትምህርት ቤት ላይ ቤንሻንጉል ጉሙዝ ሀረሪን በማሸነፍ ምድቡን በበላይነት አጠናቋል፡፡ ሀረሪዎች በፈርዶሳ ኢስማኤል የ41ኛ ደቂቃ ግብ ሲመሩ ቢቆዩም ከእረፍት በኋላ ሙሉ ለሙሉ ብልጫ የወሰዱት ቤኒሻንጉል ጉሙዞች በ62ኛው ደቂቃ አሙና ኡመር እንዲሁም በ80+1ኛው ደቂቃ መሪየም መሃመድ አማካኝነት ባስቆጠሯቸው ግቦች 2-1 አሸንፈው ወጥተዋል፡፡ ሐረሪዎች በሁለተኛው አጋማሽ ከራሳቸው የሜዳ ክልል ወጥተው ኳሰ የነኩባቸው አጋጣሚዎች በጣት የሚቆጠሩ ነበሩ፡፡
የምድብ ለ የደረጃ ሰንጠረዥ
1. ቤኒሻንጉል 2 (+2) 6
– – – – – –
2 ጋምቤላ 2 (+2) 3
3. ሐረሪ 2 (-4) 0
በተመሳሳይ ሰአት በምድብ ሐ ቢሾፍቱ ስታድየም ላይ አዲስ አበባ ከ አማራ ያደረጉት ጨዋታ 2-2 በሆነ አቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡ አዲስ አበባ በማህደር ወልዳይ የ12ኛ ደቂቃ ግብ ቀዳሚ ሲሆኑ ከ3 ደቂቃዎች በኋላ አምበሏ ሰላማዊት መኮንን አማራን አቻ አድርጋለች፡፡ በ23ኛው ደቂቃ ትዕግስት አዲሱ አማራን ወደ መሪነት ስታሸጋግር ትዕግስት ሰለሞን በ53ኛው ደቂቃ የተገኘውን የፍጹም ቅጣት ምት ወደ ግብነት ቀይራ አዲስ አበባን አቻ አድርጋለቸ፡፡ የአማራዋ ትዕግስት አዲሱ በሁለት ጨዋታ የግብ መጠኗን 5 በማድረስ የከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን በመምራት ላይ ትገኛለች፡፡
አዲስ አበባ እና አማራ አቻ መለያየታቸውን ተከትሎ በሁሉም መለኪያዎች እኩል ሆነው የምድቡ የበላይ ሆነዋል፡፡ በዚህም ወደ ግማሽ ፍጻሜው ለማለፍ በወጣው እጣ አዲስ አበባ ወደ ግማሽ ፍፃሜው ማለፍ ችሏል፡፡
የምድብ ሐ ሰንጠረዥ
1. አዲስ አበባ 2 (+5) 4
– – – – – –
2. አማራ 2 (+5) 4
3. ድሬዳዋ 2 (-10) 0
የግማሽ ፍጻሜ ተጋጣሚዎች
ኦሮምያ ከ ቤኒሻንጉል ጉሙዝ
አዲስ አበባ ከ ደቡብ
የነገ ጨዋታዎች ፕሮግራም
* ወንዶች
03:00 አዲስ አበባ ከ ድሬዳዋ (ቢሾፍቱ ስታድየም)
03:00 ኦሮምያ ከ ቤኒሻንጉል (ለምለም ተስፋ ት/ቤት)
05:00 አማራ ከ ኢትዮ ሶማሌ (ለምለም ተስፋ ት/ቤት)
05:00 ጋምቤላ ከ ደቡብ (ቢሾፍቱ ስታድየም)