ዩጋንዳዊው አማካይ ያስር ሙጌርዋ ለ2008 የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ቻምፒዮን ቅዱስ ጊዮርጊስ ለመጫወት መስማማቱን የተጫዋቹ ወኪል ለሶከር ኢትዮጵያ አረጋግጧል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ግን ስለዝውውሩ መጠናቀቅ የገለፀው ምንም ነገር የለም፡፡
ሙጌርዋ ዓመቱን በደቡብ አፍሪካ ኦርላንዶ ፖይሬትስ በመጫወት ያሳለፈ ሲሆን በዓመቱ መጨረሻ ከክለቡ ተለቋል፡፡
የሙጌርዋ ወኪል ጆኦፍሪ ካይምባ የመሃል አማካዩ ለፈረሰኞቹ የሁለት ዓመት ውል ለመፈረም መስማማቱን ለሶከር ኢትዮጵያ ተናግሯል፡፡ ዝውውሩ የተጠናቀቀ መሆኑንም ወኪሉ ጨምሮ ገልጿል፡፡
የቀድሞ ዩጋንዳ ረቨንዩ ኦቶሪቲ (ዩአርኤ) ተጫዋች ሙጌርዋ በፓይሬትስ በቂ የመሰለፍ ዕድልን የተነፈገው ሲሆን ስሙ በዝውውር መስኮቱ ከካምፓላ ሲቲ ካውንስል እና ከተለያዩ የደቡብ አፍሪካ ክለቦች ጋር ተያይዞ ሲነሳ ነበር፡፡
ኳስን ይዞ የመጫወት አቅም ያለው ሙጌርዋ ለዩጋንዳ ብሄራዊ ቡድን መጫወት ችሏል፡፡ የተከላካይ አማካይ እና የጨዋታ አቀጣጣይ መሆን የሚችለው የ22 ዓመቱ ዩጋንዳዊ በፈረሰኞቹ ቤት ከሃገሩ ልጆች ሮበርት ኦዶንካራ፣ ብራያን ኦሞኒ እና አይዛክ ኢሴንዴ ጋር የሚቀላቀል ይሆናል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ በተለይ ሰርቢያዊውን አሰልጣኝ ሰርዮቪች ‘ሚቾ’ ሚሉቲን ከ10 አመት በፊት ከቀጠረ በኃላ ወደ ክለቡ በስፋት ዩጋንዳዊንን ሲያስፈርም ይስተዋላል፡፡
[socialpoll id=”2385802″]
[socialpoll id=”2385807″]