የሴቶች እግርኳስ | 03-01-2009
በዩጋንዳ አስተናጋጅነት እየተካሄደ ባለው የሴካፋ ሴቶች ዋንጫ ከምድብ አንድ ኬንያ ወደ ግማሽ ፍፃሜ ያለፈችበት ድል ስታስመዘግብ ዩጋንዳ ዛንዚባር ላይ የግብ ናዳ አውርዳለች፡፡
ሃራምቤ ስታርሌትስ በሚል ስም የሚታወቁት ኬንያዎቹ ወደ ግማሽ ፍፃሜ ያለፉ የመጀመሪዎቹ ቡድን ሆነዋል፡፡ ቡሩንዲን 4-0 በሆነ ውጤት ባሸነፉበት ጨዋታ ኔዲ አቲኖ ኦኮት (2)፣ ማሪ ኪኑቲያ ዋንጂኩ እና ኤስ አኪዳ ግቦች ከመረብ አዋህደዋል፡፡ ቡሩንዲዎቹ ዛንዚባር ላይ ካሳዩት አቋም ባነሰ የወረደ እንቅስቃሴ ያሳዩ ሲሆን ወደ ግብ የሞከሩትም ኳስ አንድ ብቻ ነበር፡፡ ኬንያ ሁለቱንም የምድብ ጨዋታዎቾን ከጨዋታ ብልጫ ጋር ያሸነፈች ሲሆን ለቻምፒዮንነቱም ታጭታለች፡፡
ዩጋንዳ እንደተጠበቀው ዛንዚባርን በቀላሉ 9-0 ማሸነፍ ችላለች፡፡ ሁለቱም ቡድኖች ከሽንፈት እንደመምጣታቸው የሴካፋ ጉዟቸውን የቀና ለማድረግ የግድ ሶስት ነጥብ ያስፈልጋቸው ነበር፡፡ የዩጋንዳን ክረስትድ ክሬንሶችን የድል ግቦች ሃሲፋ ናሱና(4)፣ ፋዚላ ኢካዋፑት (2)፣ በዩናይትድ ስቴትስ የእግርኳስ ህይወቷን የምትመራው ላኪ ኦታንዲካ (2) እና ክርስቲያን ናምቢሪግ አስቆጥረዋል፡፡ ኢትዮጵያዊቷ ኢንተርናሽናል ረዳት ዳኛ ወይንሸት አበራ በዳኘችበት ጨዋታ ዩጋንዳዎች በመጀመሪያው አጋማሽ ለ40 ደቂቃዎች ያክል ግብ ባያስቆጥሩም በሰፊ ግብ ከማሸነፍ ያገዳቸው ነገር የለም፡፡ ዩጋንዳ ወደ ግማሽ ፍጻሜው ለማለፍ በመጪው ሃሙስ ከብሩንዲ ጋር የምታደርገው ጨዋታ ወሳኝ ነው፡፡ በሁለት ጨዋታ 19 ግብ ያስተናገደችው ዛንዚባር ከውድድሩ በግዜ ተሰናብታለች፡፡
ውድድሩ ነገም ሲቀጥል በምድብ ሁለት የምትገኘው ኢትዮጵያ ሩዋንዳን የምትገጥም ይሆናል፡፡ ሩዋንዳ ሰኞ ዕለት በታንዛኒያ 3-2 የተሸነፈች ሲሆን ኢትዮጵያ በሴቶች የሴካፋ ዋንጫ የመጀመሪያ ጨዋታዋ ይሆናል፡፡ የሁለቱ ሃገራት ጨዋታ በ10፡00 ሰዓት በንጅሩ ቴክኒካል ማዕከል የሚካሄድ ይሆናል፡፡
የፎቶ ምንጭ፡ ካዎዎ ስፖርትስ
[socialpoll id=”2385802″]
[socialpoll id=”2385807″]