ሉሲዎቹ | 03-01-2009
እሁድ በተጀመረው የሴካፋ ሴቶች ዋንጫ በምድብ ሁለት የምትገኘው ኢትዮጵያ ነገ የመጀመርያ ጨዋታዋን ከሩዋንዳ ጋር ታደርጋለች፡፡
ሉሲዎቱ ከነገው ጨዋታ በፊት የመጨረሻ ልምምዳቸውን ዛሬ ረፋድ ላይ ያከናወኑ ሲሆን ሁሉም ተጨዋቾች በሙሉ ጤንነት ላይ ይገኛሉ ተብለዋል፡፡
የብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝ መሰረት ማኒ በነገው ጨዋታ ዙርያ ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጡት አስተያየት ጨዋታው ጠንካራ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡
” ሩዋንዳ ጥሩ ቡድን ነው፡፡ ታንዛኒያ ተቸግሮ ነው ያሸነፋቸው፡፡ የነገው ጨዋታ የመጨረሻ እድላቸው ስለሆነ ጨዋታው ጠንካራ ይሆናል ” ብለዋል፡፡ አሰልጣኝ መሰረት አክለውም የሩዋንዳ እና ታንዛኒያ ጨዋታን መመልከታቸው ጠቀሜታ እንደሚኖረው ተናግረዋል፡፡
“ጨዋታውን መመልከታችን ቡድኑ ያለውን ጠንካራ እና ደካማ ጎን እንድናውቅ ይጠቅመናል ” ብለዋል፡፡
ኢትዮጵያ እና ሩዋንዳ የሚያደርጉት ጨዋታ ነገ 10:00 ላይ በኒጂሩ ቴክኒካል ማዕከል የሚካሄድ ሲሆን በዚህ ምድብ የምትገኘው ታንዛንያ አራፊ ትሆናለች፡፡