ዜና | 04-01-2009
በአዲስ አበባ እግር ኳስ ፌደሬሽን አዘጋጅነት ለ11ኛ ጊዜ የሚካሄደው የአዲስ አበባ ዋንጫ(city cup) መስከረም 28 እንደሚጀመር ታውቋል፡፡
ስምንት ክለቦችን የሚያሳትፈው ይህ ውድድር ለሁለት ሳምንታት በአዲስ አበባ ስታድየም እንደሚከናወን ከፌደሬሽኑ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ለውድድሩ በቶሎ አለመጀመር እንደ ምክንያት የቀረበው የአዲስ አበባ ስታድየም እድሳት ላይ በመሆኑ እና የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የሚጀመርበት ጊዜ በመራዘሙ እንደሆነ ፌደሬሽኑ አስታውቋል፡፡
ውድድሩ ላይ ሁሉም የአዲስ አበባ ክለቦች ማለትም ቅዱስ ጊዮርጊስ ፣ ኢትዮጵያ ቡና ፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ፣ ኤሌክትሪክ ፣ መከላከያ ፣ ደደቢት እና አዲስ አበባ ከተማ እንደሚሳተፉ የተወቀ ሲሆን አንደኛው ተጋባዥ ቡድን ግን እስካሁን እንዳልተለየ እና ምን አልባት እንደአማራጭ ከተያዙት ፋሲል ከተማ ፣ አዳማ ከተማ እና ጅማ አባ ቡና መካከል አንዱ ሊሆኑ እንደሚችል ተለልጿል፡፡ አዳማ ከተማ ባለፉት ሁለት ውድድሮች በተጋባዥነት መካፈሉ የሚታወስ ነው፡፡
ፌደሬሽኑ ለተሳታፊ ለክለቦቹ እንደየደረጃቸው የገንዘብ ሽልማት እንደ ከዚህ ቀደሙ እንደሚኖር ሲያስታውቅ የገንዘብ ክፍፍሉ ከስታድየም ትኬት ገቢ እና ከስፖንሰር ገቢ ላይ በመቶኛ ተከፋፍሎ ይደረጋል፡፡
ተሳታፊ ለሚሆኑ ክለቦች የሚከፋፈሉት ገንዘብ በመቶኛ
-አንደኛ ለሚወጣው ክለብ 15%
-ሁለተኛ ለሚወጣው ክለብ 10%
-ሶስተኛ ለሚወጣው ክለብ 7%
-አራተኛ ለሚወጣው ክለብ 4%
-አምስተኛ ለሚወጣው ክለብ 3%
-ስድስተኛ ለሚወጣው ክለብ 3% እንደሚሆን ተገልጿዋል፡፡
በኢትዮጵያ ቡና በኩል ባሳለፍነው አመት በነበረ የገንዘብ ክፍፍል ላይ ቶሎ የገንዘብ ክፍያ አልተከፈለኝም የሚል ቅሬታ እንደነበረበት ለማወቅ ቢቻልም ይህን ቅሬታ ግን ከክለቡ ጋር ውይይት በማረግ ፌደሬሽኑ እንደቀረፈው አስታውቋል፡፡
የውድድሩ የእጣ ማውጣት ስነስርዓት በሚቀጥለው ሳምንት እንደሚሆን የተገለፀ ሲሆን የውድድሩ የስያሜ ጉዳይ እስካሁን ድረስ ቁርጥ ያለ ውሳኔ አላገኘም፡፡ ውሳኔውም በሚቀጥለው ሳምንት በሚሰጥ ይፋዊ ጋዜጣዊ መግለጫ የሚገለፅ ይሆናል ተብሏል፡፡