የሴቶች እግርኳስ | 06-01-2009
የሴካፋ ሴቶች ዋንጫ የምድብ ለ የመጨረሻ ጨዋታ ዛሬ ሲካሄድ ኢትዮጵያ ከታንዛንያ ካለ ግብ አቻ ተለያይተዋል፡፡
ጨዋታው የምድቡን የበላይ የሚለይ በመሆኑ ከፍተኛ ትኩረት አግኝቶ የነበረ ሲሆን እንደተጠበቀው ጠንካራ ፉክክር አስተናግዶ ካለ ግብ ተጠናቋል፡፡ በውድድሩ ታሪክ የመጀመርያው ካለ ግብ የተጠናቀቀ ጨዋታ ሆኖም ተመዝግቧል፡፡
በጨዋታው በሁለቱም በኩል ጥቂት የግብ ሙከራዎች የተስተናገዱ ሲሆን ኢትዮጵያ በሩዋንዳው ጨዋታ የነበራትን የበላይነት ለመድገም እንደተቸገረች ከስፍራው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ጨዋታው በአቻ ውጤት መጠናቀቁን ተከትሎ የምድቡን አሸናፊ ለመለየት በወጣው እጣ ታንዛንያ አሸናፊ በመሆን የምድብ ለ የበላይ ሆና አጠናቃለች፡፡ ኢትዮጵያ በተመሳሳይ 4 ነጥብ ፣ 3 ግብ እና 1 የግብ ልዩነት በሁለተኝነት ስታጠናቀቅ ሩዋንዳ ካለምንም ነጥብ እና 2 የግብ እዳ 3ኛ ደረጃን ይዛለች፡፡
የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች እሁድ ሲደረጉ የውድድሩ ትልቅ ጨዋታ በኬንያ እነና ኢትዮጵያ መካከል ይደረጋል፡፡ ሁለቱ ለዋንጫው ከፍተኛ ግምት ያገኙ ሃገራት በመሆናቸው ጠንካራ ፉክክር ያስተናግዳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በሌላ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታ ታንዛንያ አስተናጋጇ ዩጋንዳን ትገጥማለች፡፡