የወጣቶች እግርኳስ | 10-01-2009
የኢትዮዽያ ከ17 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን ከማሊ ጋር ለሚያደርገው የአፍሪካ ከ17 አመት በታች ዋንጫ ማጣርያ ወሳኝ የመልስ ጨዋታ ዛሬ ዝግጅቱን በአዲስ አበባ ጀምሯል፡፡
ባሳለፍነው እሁድ ከማሊ ጋር ባማኮ ላይ የመጀመርያውን ጨዋታ ያደረገው ታዳጊ ቡድናችን የ2-0 ሽንፈት አስተናግዶ ትላንት አመሻሽ ላይ አዲስ አበባ የገባ ሲሆን ዛሬ የመጀመሪያ ልምምዱን በአስቸጋሪ ሁኔታዎች ውስጥ ሆኖ ኮተቤ አካባቢ በሚገኝ አነስተኛ ሜዳ ልምምዱን አከናውኗል፡፡
በልምምድ መርሃ ግብሩ ላይ 21 ተጨዋቾች የተገኙ ሲሆን ወደ ማሊ ያልተጓዙት ተጫዋቾችም ቡድኑን ተቀላቅለው ልምምድ ሲሰሩ በግብፅ ጨዋታ ላይ የነበሩት ሉክ ፖውሊን እና ሀቢብ ከቡድኑ የተቀነሱ ተጫዋቾች ናቸው፡፡
አሰለጣኝ አጥናፉ አለሙ ስለ መልሱ ጨዋታ ዝግጅት ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጡት አስተያየት የሜዳቸውን አድቫንቴጅ እንደሚጠቀሙ ተስፋ አድርገዋል፡፡ ” በማሊው የመጀመርያ ጨዋታ ላይ በነበሩብን ድክመቶች ላይ ባሉን ቀናት ውስጥ በሚገባ አስተካክለን በመግባት የሜዳ አድቨንቴጃችንን ተጠቅመን ውጤቱን እንቀለብሳለን፡፡ ወደ አፍሪካ ዋንጫው የማለፍ አላማችንንም እናሳካለን” ብለዋል፡፡
ከ2 ሳምንት በኋላ በሚደረገው የመልስ ጨዋታ በከፍተኛ የባህር ጠለል ከፍታ ላይ በምትገኘው አአ ለማድረግ የአሰልጣኞች ቡድኑ ጥያቄ ያቀረበ ሲሆን በእድሳት ላይ የሚገኘው አዲስ አበባ ስታድየምን ለጨዋታው ብቁ አድርጎ ለማድረስ በቀሩት ቀናት ጥረት ሊደረግ እንደታሰበ ሰምተናል፡፡
በኢትዮጵያ እና ማሊ መካከል የሚደረገው የመልሱ ጨዋታ መስከረም 22 በአዲስ አበባ ስቴዲዮም ይደረጋል፡፡ በድምር ውጤት የሚያሸንፈው ብሄራዊ ቡድንም ማዳጋስካር ለምታስተናግደው የአፍሪካ ከ17 አመት በታች ዋንጫ የሚያልፍ ይሆናል፡፡
በዛሬው እለት እንደታዘብነው የልምምድ ቦታው ፍጹም አመቺ ያልነበረና ወደቦታው የሚያደርሰው መንገድ አስቸጋሪ እንደነበር ታዝበናል፡፡ የመጀመርያውን ውጤት ቀልብሶ ወደ ማዳጋስካር የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ ከ2-0 በላይ በማሸነፍ ላይ የተመሰረተ እድል ይዞ የሚገባው ብሄራዊ ቡድናችን የታለመለትን ውጤት እንዲያመጣ የኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከልምምድ ሜዳ ጀምሮ አስፈላጊውን ክትትልና ድጋፍ ሊያደርግለት እንደሚገባ መልክታችን ነው፡፡