ኢትዮጵያ 1-2 ማሊ ፡ ከጨዋታው በኋላ የተሰጡ የአሰልጣኞች አስተያየቶች

የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡደን በማሊ አቻው በድምር ውጤት 4-1 ተሸንፎ ማዳጋስካር ከምታስተናግደው የ2017 ቶታል የአፍሪካ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ውጪ ሆኗል፡፡ ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱም ሃገራት አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ለጋዜጠኞች ሰጥተዋል፡፡

 

“ዳኛው በጣም በድሎናል” አጥናፉ አለሙ

ስለጨዋታው

እንቅስቃሴው ጥሩ ነው፡፡ በእኛ ደረጃ ለማሸነፍ ነው የተጫወትነው፡፡ በእግርኳስ አንዳንዴ የሚፈጠር ነው፡፡ ነገር ግን ሁሌ ማሸነፍ አትችልም፡፡ የራሳችንን ሜዳ ተጠቅመን ለማሸነፍ ሙከራ አድርገን ነበር፡፡ ያዘጋጀናቸው ወጣቶች ለወደፊቱ ብሄራዊ ቡድን ተስፋ ሊሆኑ እንደሚችሉ አይተናል፡፡ በወጣቶች ደረጃ ላይ ያሉ ውድድሮች ደግሞ እንደመማማሪያ እንደ ትምህርት ቤት ወስደን ጥሩ ቡድን ሰርተናል፡፡ የመጀመሪያው ግብ የራሳችን ስህተት ነው፡፡ ከዛ በተረፈ ያገኘናቸውን አጋጣሚዎች አልተጠቀምንም፡፡ በአንፃሩ በአካል ብቃት በልጠውናል፡፡

 

ስለትኩረት ማጣት እና መከላከል

የመከላከል ብቃታችን እና በአደረጃጀት በጣም ጥሩ ነው፡፡ ቢሆንም ስህተት ይፈጠራል፡፡ በዚህ እድሜ ደግሞ የሚጠበቅ ነው፡፡ ነገር ግን ባልጠበቅነው ሁኔታ ግብ መግባቱ ስሜታቸውን ነክቶታል፡፡ በትኩረት ማጣት ግብ ተቆጥሮብናል፡፡ ያንን ተቋቁመን ለመጫወት ሞክረናል፡፡ ነገር ግን እንዳያችሁት ዳኛው በጣም በድሎናል፡፡ ዳኛው በጣም ተጭኖናል፡፡ ሰዓቶች እንዲባክኑ አድርጓል እና የተለያዩ ነገሮች አድርጓል፡፡ ለወደፊቱ ጥሩ ትምህርት ወስደንበታል፡፡ ለልጆቹም ጥሩ የኢንተርናሽናል ልምድ ሆኗቸዋል፡፡

picsart_1475434914869

“ልምዳችን ውጤታማ አድርጎናል” ጆናስ ኮሙላ

ስለጨዋታው

ኢትዮጵያ ጥሩ ቡደን አላት፡፡ በባማኮ በነበረው ጨዋታም ጥሩ መጫወት ችለዋል፡፡ ጥሩ የእግርኳስ አቅም ያላቸው ተጫዋቾችን አሉ፡፡ ዛሬም ተጋጣሚያችን ችግር ሲፈጥርብን ነበር፡፡ ነገር ግን የልጆቼ የካበተ ልምድ ውጤታማ አድርጎናል፡፡

 

ስለዳኝነት

የዳኛው ውሳኔ የራሱ የዳኛው ነው፡፡ እኔን አይመለከተኝም፡፡ እኔን የሚመለከተኝ የራሴ ቡድን ነው፡፡

 

ዩአኪም ፊከርት ተፅእኖ በማሊ እግርኳስ…

በቴክኒኩ ደረጃ ከፊከርት ብዙ እገዛ አግኝተናል፡፡ አሁን ፊከርት ኢትዮጵያ ውስጥ ነው የሚሰራው፡፡ ከአራት ዓመታት በፊት ጥሩ ስራዎች በማሊ ሰርቶ ማለፍ ችሏል፡፡ አሁን ላይ በማሊ ብዙ የእግርኳስ አካዳሚዎችን መክፈት ችለናል፡፡

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *