ከ1985- 1994 በኢትዮጵያ ቡናና ቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫውቶ ያሳለፈው ቴዎድሮስ በቀለ (ቦካንዴ) ዛሬ ለንባብ ከበቃው ፓሽን ስፖርት መፅሄት ጋር ሰፋ ያለ ቆይታ አድርጓል፡፡
ቦካንዴ በቃለ ምልልሱ ስለ ቀድሞ እግር ኳስ ህይወቱ፣ ስለ 1990ው ኢትዮጵያ ቡና ፣ ስለ ዝውውር ሪኮርዱ ፣ ስለ ወቅታዊ ሁኔታው ፣ ስለ ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አጨዋወት እና ስለ ታዳጊው ጌድዮን ዘላለም አውግቷል፡፡ እኛም ሙሉውን ቃለምልልስ ከመፅሄቱ እንድታነቡ እየጋበዝን ለሶከር ኢትዮጵያ ተከታታዮች በሚመች መልኩ ጠቂቱን መርጠን እንዲህ አቅርበነዋል፡፡
ስለ ጌድዮን ዘላለም
‹‹ ሰሜን ለንደን ዱከም የሚባል ሬስቶራንት አለ፡፡ አብዛኛውን ጊዜ ከአባቱ ጋር እየመጣ ሲመገብ አገኘዋለሁ፡፡ከኢትዮጵያ ምግቦች ሁሉ ለክትፎ ልዩ ፍቅር አለው፡፡ በኢትዮጵያዊነቱ በጣም ይኮራል፡፡ ለዛም ነው የሀበሻ ሬስቶራንት የሚያዘወትረው፡፡ጀርመን እና ዩናይትድ ስቴትስ እንዲጫወቱለት ጥያቄ ቢያቀርቡም ኢትዮፕያን እንደሚወዳት በተግባር አረጋግጫለሁ፡፡ የእግርኳስ ፌዴሬሽኑ እና አሰልጣኙ ታዳጊውን ለማግባባት ጥረት ቢያደርጉ ጥሩ ነው፡፡››
(አሰልጣኝ ሰውነት መጫወት ከፈለገ ይደውልልን ስለማለታቸው)
‹‹አሉ እንዴ … ከባድ ነው ፡፡ ሁሉም አሰልጣኝ የየራሱ አካሄድ ቢኖረውም ኳስ የሚችል ተጫዋችን ማግኘት የምትችለው ፈልገኸው እንጂ እስኪደውልልህ ጠብቀህ አይደለም፡፡ ››
ስለ ብሄራዊ ቡድኑ የቻን ውጤት
‹‹ አብዛኛዎቹ ይዘው የመጡት ሁለተኛ ቡድናቸውን ነው፡፡ ይሁንና አሁንም መናገር የምፈልገው በተጫዋቾቹ ላይ ሳይሆን በአጨዋወቱ ላይ ነው፡፡አሰልጣኙ ይዞ ስለሚገባው አጨዋወት በሚገባ ማወቅ አለበት፡፡በሊቢያው ጨዋታ ላይ አስራት መገርሳ የተከላካይ አማካይ ይሁን የአጥቂ አማካይ አይታወቅም፤አዳነ ወደፊት ሲሄድ ሰፊ ክፍተት ይተዋል፤ኡመድ ተነጥሎ ነበር… ከጋና ጋር የተሸለ ነገር ብመለከትም ኳስ መበላሸት ሲጀምር እንደገና ወደረጃጅም ኳሶች ሲበገቡ ተመልክቻለሁ፡፡
ማድረግ የሚገባቸው ኳሱን ከኋላ መስርቶ መጫወት ነው፡፡ አንድ ሁለቴ ቢበላሽ እንኳን በትግስት መደጋገም አለብህ፡፡ አለበለዚያ በቀላሉ ተጋጣሚህ ወደሚፈልገው አጨዋወት ትገባለታለህ፡፡ ኳስ ከኋላ መስርቶ ለመጫወት ደግሞ እንደ ሳሙኤል ደምሴ(ኩኩሻ) አይነት የተረጋጋ እና በራስ መተማመን ያለው ተከላካይ በተከላካይ መስመርህ ላይ ልትይዝ ይገባል፡፡
ስለ ካሳዬ አራጌ
ከሱ ጎን በመጫወቴ ተጠቅሜያለው፡፡የኢትዮጵያን እግርኳስ የመቀየር አቅም ያለው ባለሙያ ነው፡፡ዛሬ ባርሴሎና የሚተገብረውን አጨዋወት ከ15 አመት በፊት ካሳዬ ተግብሮት ነበር፡፡ኳሱን ወደኋላ በመለስክ ቁጥር የተጋጣሚ ተከላካዮች ወደአንተ ግብ ክልል ይጠጋሉ ፤ በዚህም ክፍተት ታገኛለህ ፤ ሊነጥቁህ ሲጠጉህ እያፈተለክ ታጠቃለህ፡፡