የ2009 የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ፣ ብሄራዊ ሊግ ፣ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ እና ከ20 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ የእጣ ማውጣት ስነስርአቶች በቀጣዩ ሳምንት እንደሚካሄዱ ታውቋል፡፡
ጥቅምት 3 ሊካሄድ የታሰበው የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ በታሰበበት ቀን መካሄድ ያልቻለ ሲሆን በመጪው ሰኞ ጥቅምት 15 ቀን 2009 እንዲካሄድ ተወስኗል፡፡ ህዳር 3 እንደሚጀመር አስቀድሞ የተወሰነው ከፍተኛ ሊጉ የሚጀመርበት ቀን ይራዘም አይራዘም የታወቀ ነገር የለም፡፡
የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ጥቅምት 8 እጣ እንዲወጣ ታስቦ የነበረ ቢሆንም በ8 ቀናት ወደፊት ተገፍቶ ማክሰኞ ጥቅምት 16 እንዲካሄድ ተወስኗል፡፡ ለመጀመርያ ጊዜ የሚካሄደው የ20 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ ደግሞ ጥቅምት 11 ሊካሄድ የነበረው ወደ ጥቅምት 16 አንዲሸጋሸግ ተደርጓል፡፡ በዚህም ከ17 እና ከ20 አመት በታች ሊጎች በተመሳሳይ ቀን እጣ የሚወጣ ይሆናል፡፡
ከትላንት በስቲያ ሊካሄድ የነበረው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ሊግ የእጣ ማውታት ስነስርአት ወደ አርብ ጥቅምት 18 ቀን 2009 ተሸጋግሯል፡፡
በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ስር ከሚካሄዱት የሊግ ወድድሮች መካከል የኢትዮጵያ ወንዶች እና ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እጣ የወጣ ሲሆን የቀሪዎቹ ከላ በተጠቀሱት ቀናት ከተካሄዱ በኋላ ውድድሮቹ የሚጀመሩባቸው ቀናት ለውጥ ደረግባቸው አይደረግባቸው የሚታወቅ ይሆናል፡፡
ፌዴሬሽኑ ከዚህ ቀደም ይፋ ያደረጋቸው የሊጎች መጀመርያ ቀናት የሚከተሉት ናቸው፡–
ፕሪሚየር ሊግ – ጥቅምት 20
ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ – ህዳር 11
ከፍተኛ ሊግ – ህዳር 3
ብሄራዊ ሊግ – ህዳር 11
ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ – ህዳር 11
ከ20 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ – ህዳር 18