በአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ምድብ ለ ትላንት የተደረጉት ሁለቱም ጨዋታዎች ያለግብ በአቻ ውጤት ተጠናቀዋል፡፡
09፡00 ላይ በመጀመርያው ጨዋታ ሽንፈት ያስተናገዱት ደደቢት እና አዲስ አበባ ከተማ ያለ ግብ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ተመጣጣኝ እንቅስቃሴ በታየበት ጨዋታ ደደቢት ከመጀመርያው ጨዋታ በተሻለ ቋሚ ተሰላፊዎቹን የተጠቀመ ሲሆን አዲስ አበባ ከተማ በተለይም በመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች የፈጠሯቸውን የግብ እድሎች መጠቀም አልቻሉም፡፡
11፡00 ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ አዳማ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ በተመሳሳይ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡ አልፎ አልፎ ከሚደረጉት ኢላማቸውን ያጠበቁ የግብ ሙከራዎች ውጪ ጨዋታው ያን ያህል ትኩረት ሳቢ አልነበረም፡፡ ሁለቱ ቡድኖች የመጀመርያውን ጨዋታ ማሸነፋቸውን ተከትሎ ወደ ግማሽ ፍፃሜው ተያይዘው የማለፍ እድላቸውን አስፍተዋል፡፡
ምድቡን አዳማ ከተማ በ4 ነጥብ እና 3 የግብ ልዩነት ሲመራ ንግድ ባንክ በተመሳሳይ ነጥብ እና በ1 የግብ ልዩነት ይከተላል፡፡ አዲስ አበባ ከተማ እና ደደቢት 1 ነጥብ ይዘዋል፡፡
የከተማው ዋንጫ ጨዋታዎች ከአንድ ቀን እረፍት በኋላ ነገ ሲቀጥሉ በምድብ ሀ የመጨረሻ ጨዋታዎች 09፡00 ላይ ኢት-ኤሌክትሪክ ከ ማ አባ ቡና ፣ 11፡00 ላይ መከላከያ ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ ይጫወታሉ፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከዚህ ምድብ አስቀድሞ በማለፉ የሚጠበቀው ተከታዩ አላፊ ቡድን ነው፡፡