ቅዳሜ የተጀመረው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ እሁድ ቀጥሎ ሲውል አዳማ ፣ ደደቢት ፣ አአ ፣ ድቻ ፣ ወልድያ እና ሲዳማ በድል የውድድር ዘመናቸውን ከፍተዋል፡፡
ወደ ሀዋሳ ያቀናው አዲስ አበባ ከተማ ባለሜዳው ሀዋሳ ከተማን ባልተጠበቀ ሁኔታ 2-0 አሸንፏል፡፡ ለአዲስ አበባ ከተማ የድል ግቦቹን ከእረፍት መልስ በ51ኛው ደቂቃ ኃይለየሱስ መልካ እና በ71ኛው ደቂቃ ፍቃዱ አለሙ አስቆጥረዋል፡፡ በታሪክ የመጀመርያ የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ያደረገው ድሉ ለዋና ከተማው ክለብ ከሜዳው ውጪ የመጀመርያውን ግብ እና 3 ነጥብ ማስመዝገብ ችሏል፡፡
ወላይታ ድቻ የሶዶ ስታድየምን በድል ከፍቷል፡፡ የወላይታ ድቻን የድል ግቦች ከመረብ ያሳረፉት በዛብህ መለዮ በ55ኛው ደቂቃእናአላዛር ፋሲካ በ73ኛው ደቂቃ ናቸው፡፡ በዚህ ጨዋታ 24ኛው ደቂቃ ላይ የመከላከያው ተከላካይ አወል አብደላ በቀይ ካርድ ከሜዳ የተወገደ ሲሆን የውድድር ዘመኑ የመጀመርያ ቀይ ካርድ ሆኖም ተመዝግቧል፡፡
ይርጋለም ላይ ሲዳማ ቡና ፋሲል ከተማን አስተናግዶ 1-0 አሸንፏል፡፡ በክረምቱ ክለቡን የተቀላቀለው ትርታዬ ደመቀ በ28ኛው ደቂቃ ብቸኛዋን የማሸነፍያ ግብ አስቆጥሯል፡፡ በዚህ ጨዋታ የ2008 የከፍተኛ ሊጉ ኮከብ ተጫዋች አብዱራህማን ሙባረክ በ2 ቢጫ ከሜዳ ተሰናብቷል፡፡
አዳማ አበበ ቢቂላ ላይ አዳማ ከተማ ድሬዳዋ ከተማን አስተናግዶ 1-0 አሸንፏል፡፡ የአዳማን ወሳኝ የድል ግብ አምበሉ ሱሌይማን መሃመድ በ60ኛው ደቂቃ በቅጣት ምት አስቆጥሯል፡፡
ጅማ ላይ ጅማ አባ ቡና በታሪኩ የመጀመርያውን የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ከኢትዮ ኤሌክትሪክ አድርጎ ያለግብ በአቻ ውጤት ፈጽሟል፡፡ ጨዋታው በሞበ የደጋፊ ድባብ ቢካሄድም የተጠበቀውን ያህል እንቅስቃሴ ሳይደረግበት ቀርቷል፡፡ ኢትዮ ኤሌክትሪኮች በርካታ ተጫዋቾች በመጎዳታቸው 16 ተጫዋቾችን ይዞ ወደ ጅማ ለመሄድ ተገዷል፡፡
አዲስ አዳጊው ወልድያ የውድድር ዘመኑን በድል ከፍቷል፡፡ መልካ ቆሌ ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ያስተናገደው ወልድያ አንዱአለም ንጉሴ በ64ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ግብ 1-0 ማሸነፍ ችሏል፡፡
በጉጉት ሲጠበቅ የነበረው የኢትዮጵያ ቡና እና የደደቢት ጨዋታ በደደቢት 3-0 የበላይነት ተጠናቋል፡፡ ጌታነህ ጎልቶ በወጣበት ጨዋታ ሶስቱንም የድል ግቦች አስቆጥሮ ሐት-ትሪክ ሰርቷል፡፡ በ15ኛው ደቂቃ ሀሪሰን ሄሱ ከፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውጪ ኳስ በእጅ በመንካቱ በቀጥታ ቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል፡፡
ቅዳሜ በተካሄደው የመክፈቻ ጨዋታ የአምናው ቻምፒዮን ቅዱስ ጊዮርጊስ በአቡበከር ሳኒ ፣ ሳላዲን ሰኢድ እና አዳነ ግርማ ግቦች አርባምንጭ ከተማን 3-0 አሸንፏል፡፡
በአጠቃላይ በ1ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ከተደረጉት 8 ጨዋታዎች 7ቱ በመሸናነፍ ሲጠናቀቁ 13 ግቦች ተቆጥረዋል፡፡ አርቢቴር ኀይለየሱስ ባዘዘው የውድድር ዘመኑን መጀመር የሚያበስረውን ፊሽካ ካሰሙ በኋላ ፈጣኑ ግብ በአቡበከር ሳኒ (30 ሴኮንድ) ሲመዘገብ ጌታነህ የመጀመርያውን ሐት-ትሪክ አስመዝግቧል፡፡ ምንያህል ተሾመ የመጀመሪያው የማስጠንቀቂያ ካርድ ሲመዘዝበት አወል አብደላ ደግሞ የመጀመርያው የቀይ ካርድ ሰለባ ሆኗል፡፡
የደረጃ ሰንጠረዥ
ከፍተኛ ግብ አግቢዎች
የ2ኛ ሳምንት ፕሮግራም
ቅዳሜ ህዳር 10 ቀን 2009
09፡00 ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ ሀዋሳ ከተማ (አአ)
11፡30 መከላከያ ከ ኢትዮጵያ ቡና (አአ)
እሁድ ህዳር 11 ቀን 2009
09፡00 አዲስ አበባ ከተማ ከ ጅማ አባ ቡና (አአ)
09፡00 አርባምንጭ ከተማ ከ ወልድያ (አርባምንጭ)
09፡00 ፋሲል ከተማ ከ ወላይታ ድቻ (ፋሲለደስ)
09፡00 አዳማ ከተማ ከ ሲዳማ ቡና (አዳማ)
10፡00 ድሬዳዋ ከተማ ከ ኢትዮ ኤሌክትሪክ (ድሬዳዋ)
11፡30 ደደቢት ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ (አአ)