ኢትዮጵያዊው ኢንተርናሽናል ዳኛ በአምላክ ተሰማ በጃንዋሪ 2017 በጋቦን አስተናጋጅነት በሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ከሚዳኙ ዳኞች አንዱ ሆኖ በካፍ ተመርጧል፡፡ በአፍሪካ ዋንጫው እንዲዳኙ ከተመረጡት መካከል በአምላክ ብቸኛው ኢትዮጵያዊም ሆኗል፡፡
በአምላክ ተሰማ በርካታ የአፍሪካ ቻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ጨዋታዎች እንዲሁም የሀገር ውስጥ ሊጎች ውስጥ የሚጫወቱ ተጫዋቾች በሚወዳደሩበት ቻን ውድድር ላይ ጨዋታዎችን የመራ ሲሆን በአፍሪካ ዋንጫ ጨዋታዎችን እንዲመራ ሲመረጥ ለ2ኛ ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በ2015 የኢኳቶርያል ጊኒ የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በምድብ መ ካሜሩን ከ ጊኒ 1-1 ያጠናቀቁትን ጨዋታ በዳኝነት መምራቱ የሚታወስ ነው፡፡
በካፍ ከፍተኛው የዳኞች ደረጃ ‹‹ኤ ሊስት›› ውስጥ የተካተተ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ዳኛ የሆነው በአምላክ አዳዲስ ዳኝነትን የሚያግዙ የቴክኖሎጂ ውጤቶችን ለሃገራችን በማስተዋወቅ የሚታወቅ ሲሆን ሰሞኑን ለአፍሪካ ዋንጫው ጠንካራ ዝግጅት በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡