የውድድር ዘመኑ ሁለተኛ አጋማሽ እያንዳንዱ ጨዋታዎች ለመብራት ኃይል የፍፃሜ ጨዋታ ያህል ናቸው፡፡ የማይዘሙት ምሰሶዎች ነገ ከሀዋሳ ከነማ ጋር የሚያደርጉት ጨዋታ ከእረፍት መልስ ምን አይነት ቡድን ይዘው እንደሚመጡ የሚጠቁም ይሆናል፡፡ ባለፉት 2 አመታት በአሰልጣኝ ቅጥር ላይ መረጋጋት ያልቻሉት ሀዋሳ ከነማዎችም ቢሆን በአዲስ አሰልጣኝ ምን ሊመስሉ እንደሚችሉ የምንገመግምበት ጨዋታ ይሆናል፡፡
ሁለቱ ቡድኖች በአንደኛው ዙር የመጀመርያ ጨዋታ ሀዋሳ ላይ ሲገናኙ የተመዘገበው ውጤት የአሁን ደረጃቸውን የሚገልፅ አልነበረም፡፡ መብራት ኃይል ጨዋውን በአሸናፊነት ሲወጣ አሰልጣኙ ዮርዳን ስቶይኮቭ ሳይቀሩ ስብስቤ ዋንጫ የመውሰድ አቅም አለው እስከማለት ደርሰው ነበር፡፡ በትልቅ ደረጃ የማሰልጠን ልምድ በሌላቸው አሰልጣኝ በፍቃዱ ዘሪሁን መሪነት የውድድር ዘመኑን የጀመሩት ሀዋሳ ከነማዎች ደግሞ በጨዋታው ከተሸነፉ በኋላ የውድድር ዘመኑ ሊከብዳቸው እንደሚችል ተገምቶ ነበር፡፡ አሁን ሁለተኛው ዙር ተጀምሮ ሁለቱ ቡድኖች ያሉበት ሁኔታን ስንመለከት ግምቶች መፋለሳቸውን እንረዳለን፡፡ መብራት ኃይል በወራጅ ቀጠና ሲዳክር ሀዋሳ ከነማ አሁን በ9ኛ ደረጃ ላይ ቢቀመጥም በመሃል መሻሻል አሳይቶ ነበር፡፡
ሁለቱም የዘንድሮ መጥፎ ሪከርዳቸውን ለማሻሻል ይጫወታሉ
አሰልጣኝ በፍቃዱ ዘሪሁንን ወደ ምክትል አሰልጣኝነት አውርደው የቀድሞ የክለባቸው ተጫዋች የነበሩት አሰልጣኝ ታረቀኝ አሰፋን የቀጠሩት ሀዋሳ ከነማዎች ዘንድሮ ከአዲስ አበባ ክለቦች ጋር በሜዳቸውም ሆነ ከሜዳቸው ውጪ ማሸነፍ ተስኗቸዋል፡፡ በመብራት ኃይል ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ኢትዮጵያ ቡና እና ንግድ ባንክ ሲረቱ ከመከላከያ እና መድን ጋር አቻ ተለያይተዋል፡፡ የዮርዳን ስቶይኮቭ ቡድንም ከደቡብ ክለቦች ጋር ተጫውቶ ማሸነፍ የቻለው የነገ ተጋጣሚውን ብቻ ነው፡፡ ከድቻ ጋር አቻ ሲወጣ በሲዳማ ቡና እና አርባምንጭ ከነማ ተሸንፏል፡፡
እውነታዎች
ሀዋሳ ከነማ ከ4 ተከታታይ ሽንፈቶች በኋላ ወደ አሸናፊነት ለመመለስ መብራት ኃይሎች ደግሞ የውድድር ዘመኑን 3ኛ ድል ለማስመዝገብ ይጫወታሉ፡፡
ሁለቱ ቡድኖች ከ13 አመት በፊት በተመሳሳይ 14ኛው ሳምንት ላይ ተገናኝተው ነበር፡፡ ሀዋሳ ላይ በተደረገው ጨዋታ ካለ ግብ 0-0 አቻ ተለያይተዋል፡፡
መብራት ኃይል ከ ሀዋሳ ከነማ ጋር በሜዳው ያደረጋቸውን ያለፉት 3 ተከታታይ ጨዋታዎች አሸንፏል፡፡
የእርስ በእርስ ግንኙነት ሪኮርዶች
በአጠቃላይ |
አዲስ አበባ ላይ |
ተጫወቱ – 31 (44 ግቦች) |
ተጫወቱ – 16 |
መብራት ኃይል አሸነፈ – 12 |
መብራት ኃይል አሸነፈ – 8 (25 ግቦች) |
አቻ – 8 |
አቻ – 3 |
ሀዋሳ ከነማ አሸነፈ – 11 (37 ግቦች) |
ሀዋሳ ከነማ አሸነፈ – 5 (16 ግቦች) |