አሰልጣን ጎራን ስቲቫኖቪች በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ቴክኒክ ኮሚቴ መስፈርቶች በመመረጣቸው ለድርድር አዲስ አበባ እንዲመጡ ተጋብዘው ትላንት አዲስ አበባ ገብተው ነበር፡፡ ትላንት ማምሻውን እና ዛሬ ረፋድ በተደገሩ ድርድርሮች ግን እንደተጠበቀው ስምምነት ላይ ሊደርሱ አልቻሉም፡፡
ፌዴሽኑ ዛሬ ለመገናኛ ብዙሃን በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው ጎራን እና ፌዴሬሽኑ በሶስት መሰረታዊ ጉዳዮች ላይ ስምምነት ላይ ሊደርሱ ባለመቻላቸው ድርድሩ ተቋርጧል፡፡ከስምምነት እንዳይደርሱ እንቅፋት የሆኑት በአሰልጣኝ ጎራን ቡል የቀረቡት የቤተሰብ ፣ የኮቺንግ ስታፍ እና የደሞዝ መጠን ላይ ነው፡፡
አሰልጣኙ ከቤተሰባቸው ጋር በተያያዘ ችግር እንዳጋጠማቸው ገልፀው ቤተሰቦቻቸው እዚህ መምጣት ስለማይችሉ ከአዲስ አበባ – ቤልግሬድ እየተመላለሱ ዋልያዎቹን ለማሰልጠን ጠይቀዋል፡፡
አሰልጣኙ የአሰልጣኝ ቡድኑን ከውጪ በሚያመጧቸው ባለሙያዎች ለማወቀር የጠየቁ ሲሆን በደሞዝ ጉዳይ ደግሞ አሰልጣኙ እነዲከፈላቸው የፈለጉት 30 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ፣ ለምክትል አሰልጣኙ እና የአካል ብቃት አሰልጣኙ ደግሞ እያንዳንዳቸው 10 ሺህ የአሜሪካን ዶላር ነው፡፡
ፌዴሬሽኑም በሶስቱም ጉዳዮች ላይ ያለውን አቋም አሳውቋል፡፡ አሰልጣኙ በብሄራዊ ቡድኑ ስራ ሙሉ ትኩረታቸውን እንዲያደርጉና ከአዲስ አበባ – ቤልግሬድ የሚመላለሱበት ወጪ ከፍተኛ በመሆኑ ፤ ያቀረቡት የደሞዝ ጥያቄ ከፍተኛ በመሆኑ እንዲሁም የአሰልጣኝ ቡድኑን በሃገር ውስጥ ባለሙያዎች በማዋቀር የእውቀት ሽግግር ለማድረግ በማለም ጠያቄዎቻቸውን ውድቅ አድርጓል፡፡
የጎራን እና የፌዴሬሽኑን ሳይስማሙ መለያየት ተከትሎ ፌዴሬሽኑ ለብሄራዊ ቡድኑ አሰልጣኝነት በእጩነት ይዟቸው ወደነበሩት ፖርቱጋላዊው ማርያኖ ባሬቶ ፣ ስዊድናዊው ላርስ ኦልፍ እና ሰርብያዊው ዞራን ፊሊፖቪች ፊቱን አዙሯል፡፡
{jcomments on}