ከፍተኛ ሊግ | ውሃ ስፖርት በግብ ሲንበሸበሽ መድን ደረጃውን ያሻሻለበትን ድል አስመዝግቧል 

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ 14ኛ ሳምንት የመጀመሪያ ቀን ውሎ ዛሬ በአበበ ቢቂላ ስታዲየም ሁለት የምድብ ሀ ጨዋታዎች ተካሂደው ኢትዮጵያ መድን ሰበታ ከተማን ፣ ኢትዮጲያ ውሃ ስፖርት ሽረ እንዳስላሴን አሸንፈዋል፡፡

በቅድሚያ በ8፡00 ሰአት እንዲደረግ ቀጠሮ ተይዞለት የነበረው የኢትዮጵያ መድን እና የሰበታ ከተማ ጨዋታ 38 ያክል ደቂቃዎች ዘግይቶ የተጀመረ ሲሆን ኢትዮጵያ መድኖች በጨዋታው ጥሩ እንቅስቃሴን ያሳየው የመስመር ተጫዋቹ አብይ ቡልቲ በ74ኛው ደቂቃ ባስቆጠራት ብቸኛ ግብ ሰበታ ከተማን 1-0 ማሸነፍ ችሏል፡፡

በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ የተሻለ መንቀሳቀስ የቻሉት ኢትዮጵያ መድኖች በተሻለ ወደ ግብ በመቅረብ የግብ ሙከራዎችን ማድረግ ችለው ነበር በተለይም በ37ኛው ደቂቃ በመልሶ ማጥቃት ከቀኝ መስመር አብይ ቡልቲ ወደ መሀል ያቀበለውን ኳስ ሀብታሙ ረጋሳ ሞክሮ የግቡ ቋሚ የመለሰበት ኳስ የምትጠቀስ ነበረች፡፡

በሁለተኛው አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች በንፅፅር ከመጀመሪያው የተሻለ ፉክክር አሳይተዋል፡፡ በ56ኛው ደቂቃ ላይ ሰበታ ከተማዎች በሁለተኛው አጋማሽ ተቀይሮ የገባው ፋሲል ባቱ ያቀበለውን ኳስ አጥቂያቸው ዮሴፍ በቀለ ቢያስቆጥሩም የመስመር ዳኛው ሳያፀድቀው ቀርቷል፡፡

በ74ኛው ደቂቃ ላይ መድኖች በአብይ ቡልቲ ባስቆጠሯት አንድ ግብ መምራት ቢችሉም ሰበታ ከተማዎች አቻ መሆን የሚችሉበትን እድሎች በ76ኛው ደቂቃ ላይ ተቀይሮ የገባው የፊት አጥቂው በግንባር በመግጨት ሞክሮ ያመከናት እንዲሁም በ80ኛው ደቂቃ ላይ ዮናስ አርአያ ከረጅም ርቀት ሞክሮ ለጥቂት ከግቡ አናት በላይ የወጣችበት ኳስ የሚያስቆጩ አጋጣሚዎች ነበሩ፡፡

ድሉን ተከትሎ በሻምበል መላኩ የሚመሩት ኢትዮጵያ መድኖች ነጥባቸውን ወደ 20 በማሳደግ ነገ ጨዋታውን የሚያደርገው ባህርዳር ከተማን በግብ ልዩነት በመቅደም 3ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡

በመቀጠል በተደረገው ጨዋታ ኢትዮጲያ ውሃ ስፖርት ሽረ እንዳስላሴ ላይ እጅግ ፍፁም የሆነ የጨዋታ የበላይነት አሳይቶ 5-1 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡

በመጀመሪያው አጋማሽ ላይ ኢትዮጵያ ውሃ ስፖርቶች ከተጋጣሚያቸው በተሻለ ኳስን መቆጣጠር ቢችሉም በጥልቀት ሲከላከሉ የነበሩትን ሽረዎችን ለማለፍ ሲቸገሩ ተስተውሏል፡፡ ነገርግን ከፍተኛ ጫና መፍጠራቸውን የቀጠሉት ውሃ ስፖርቶች በ36ኛው እና በ39ኛው ደቂቃ ላይ የጨዋታው ኮከብ በነበረው ውብሸት ካሳዬ ባስቆጠራቸው ሁለት ግቦች የመጀመሪያውን አጋማሽ በ2-0 መሪነት ማጠናቀቅ ችለዋል፡፡ በ40ኛው ደቂቃ አዲስዓለም ደሳለኝ ከርቀት አክርሮ ሞክሮ የግቡ ቋሚ የመለሰበት ኳስ እንዲሁም በተጨማሪ ደቂቃ ቀፀላ ፍቅረማርያም ያመከናት ፍፁም ግልፅ የማግባት አጋጣሚን መጠቀም ቢችሉ በመጀመሪያው አጋማሽ የነበራቸው መሪነት ከዚህም በላይ መስፋት ይችል ነበር፡፡

በሁለተኛው አጋማሽ እንደመጀመሪያው ሁሉ ውሃ ስፖርቶች ከጨዋታው ጅማሮ አንስቶ ቶሎ ቶሎ ወደግብ መድረስ ችለዋል፡፡ በ51ኛው ደቂቃ ላይ አባይነህ ፋኖ እንዲሁም በ55ኛው ደቂቃ ውብሸት ካሳዬ ሶስታ ሊሰራበት የሚችልበትን አጋጣሚ በተመሳሳይ ከሽረ ግብጠባቂ ጋር 1ለ1 ተገናኝተው ያመከኗቸው ኳሶች ተጠቃሽ አጋጣሚዎች ነበሩ፡፡ ነገርግን የኃላ ኃላ በ60ኛው ደቂቃ ላይ ደሳለኝ ወርቁ በግሩም ሆኔታ ተመስርቶ የመጣውን ኳስ አክርሮ በመምታት መሪነቱን ወደ 3-0 አስፍቷል፡፡

በ77ኛው ደቂቃ ውብሸት ካሳዬን ተክቶ የገባው ክብረአብ ማቱሳላ በግንባር በመግጨት 4ኛውን ግሩም ግብ ሲያስቆጥር በ82ኛው ደቂቃ ላይ ብርሃኔ አንለይ የቡድኑን የማሳረጊያ ግብ አስቆጥሯል፡፡

በቀድሞው የብሄራዊ ቡድን እና ደደቢት ረዳት አሰልጣኝ ዳንኤል ጸሀዬ የሚመሩት ሽረዎች የፊት አጥቂያቸው ቢኒያም ሀዱሽ በግሉ ከሚያደርገው ጥረት ውጪ ይህ ነው የሚባል ነገር ማሳየት አልቻሉም፡፡ ሆኖም በ84ኛው ደቂቃ በሰኢድ ሁሴን ከባዶ መሸነፍ የዳኑበትን ግብ አስቆጥረው ጨዋታው በኢትዮጵያ ውሃ ስፖርት የ5-1 አሸናፊነት ተጠናቋል፡፡

ኢትዮጵያ ውሃ ስፖርት ድሉን ተከትሎ በ18 ነጥብ 5ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል፡፡

 

ምድብ ሀ

[table id=208 /]

[league_table 18186]

ምድብ ለ

[table id=210 /]

[league_table 18205]

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *