በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ 15ኛ ሳምንት መርሃ ግብር ዛሬ በተደረጉ ጨዋታዎች ተጀምሯል፡፡ የምድብ ሀ መሪው ደደቢት የምድቡ ግርጌ ላይ የተቀመጠው ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ላይ የግብ ናዳ ሲያዘንብ አዲስ አበባ ከተማ ልደታ ክፍለ ከተማን እንዲሁም ኢትዮ ኤሌክትሪክ ኢትዮጵያ ቡናን አሸንፈዋል፡፡
በእለቱ የመጀመሪያ ጨዋታ በነበረውና በምድብ ለ የሚገኙት ልደታ ክፍለ ከተማን ከአዲስ አበባ ከተማ ባገናኘው ጨዋታ አዲስ አበባዎች 2-0 በሆነ ውጤት ማሸነፍ ችለዋል፡፡
ተመጣጣኝ ፉክክር በታየበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ከሰሞኑ ጥሩ አቋሟን እያሳየች የምትገኘው አስራት አለሙ በጨዋታው የመጀመሪያ ደቂቃዎች አከታትላ ባስቆጠረቻቸው ሁለት ግቦች ጨዋታውን አሸንፈው መውጣት ችለዋል፡፡
የዛሬውን ድል ተከትሎ አዲስአበባ ከተማ በ22ነጥብ ሲዳማ ቡና ጨዋታውን እስኪያደርግ ድረስ በ5ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችሏል፡፡
በመቀጠል የተገናኙት በምድብ ሀ ከአናት እና ግርጌ የተቀመጡት ደደቢት እና ንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ነበሩ፡፡ በጨዋታውም ደደቢት በቀላሉ 8-0 በሆነ ውጤት አሸንፏል፡፡
በጨዋታው የመጀመሪያ አጋማሽ ንፋስ ስልኮች የደደቢት አጥቂዎችን በተለይም ሎዛ አበራን በተደጋጋሚ ከጨዋታ ውጪ ወጥመዳቸው ውስጥ በማስገባት በመጀመሪያው አጋማሽ ለተወሰኑ ደቂቃዎች ግብ ሳያስተናግዱ ቆይተው ነበር፡፡ ነገር ግን በመጀመሪያው አጋማሽ መገባደጃ ደቂቃዎች ላይ ጎል አነፍናፊዋ ሎዛ አበራና ትበይን መስፍን ባስቆጠሯቸው ግቦች በደደቢት 2-0 መሪነት ወደ እረፍት አምርተዋል፡፡
ከእረፍት መልስ ደደቢቶች በጨዋታው ሙሉ የጨዋታ የበላይነት ወስደው ተጨማሪ ስድስት ግቦችን አክለው ጨዋታው 8-0 ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡ ሎዛ አበራ በሁለተኛው አጋማሽ ተጨማሪ ሶስት ግቦችን አስቆጥራ በሊጉ ያስቆጠረቻቸውን ግቦች መጠን ወደ 26 ከፍ ስታደርግ ቀሪዎችን ግቦች ብርቱካን ገ/ክርስቶስ 2 እንዲሁምን ሰናይት ቦጋለ አንድ አስቆጥራለች፡፡
በንፋስ ስልክ በኩል በሁለተኛው አጋማሽ ጅማሮ የግብ ጠባቂ ለውጥ በማድረጋቸው በ84ኛው ደቂቃ ተቀይራ የገባችው ግብ ጠባቂ በጉዳት ከሜዳ በመውጣቷ ቀሪዎቹን ደቂቃ ከሜዳ ላይ ተጫዋቾች አንድዋን ወደ ግብ ጠባቂነት ቀይረው ለመጫወት ተገደዋል፡፡
በእለቱ የመጨረሻ ጨዋታ አመሻሽ 11:30 ላይ በምድብ ሀ የሚገኙትን ኢትዮ ኤሌክትሪክና ኢትዮጵያ ቡና ባደረጉት ጨዋታ ኢትዮ ኤሌክሪክ ለተከታታይ ሁለተኛ ሳምንት ከመመራት ተነስቶ 2-1 ማሸነፍ ችሏል፡፡
ጠንካራ ፉክክር በታየበት ዝናባማው የመጀመሪያ አጋማሽ ኢትዮጵያ ቡና በድንቅነሽ ላቀው አማካኝነት ባስቆጠረችው ግብ መምራት ቢችልም መሪነታቸው መዝለቅ የቻለው ለ3 ያክል ደቂቃዎች ብቻ ነበር፡፡ ኢትዮ ኤሌክትሪኮች በአይናለም ጸጋዬ አማካይነት ወዲያውኑ አቻ መሆን ችለዋል፡፡
በጨዋታው የሁለተኛ አጋማሽ 51ኛው ደቂቃ ላይ የስታዲየሙ ባውዛ በመጥፋቱ ጨዋታው ለ21 ያክል ደቂቃዎች ከተቋረጠ በኃላ መብራቱ ዳግም በመምጣቱ ጨዋታው ሊቀጥል ችሏል፡፡ በሁለተኛው አጋማሽ ብልጫ ወስደው መጫወት የቻሉት ኤሌክትሪኮችም በአንበላቸው ፅዮን ፈየራ ግብ ከመመራት ተነስተው ማሸነፍ ችለዋል፡፡
አሸናፊዎቹ ኤሌክትሪኮች ነጥባቸውን ወደ 26 አሳድገው ድሬዳዋ ከተማና መከላከያ ጨዋታቸውን እስኪያደርጉ ድረስ በ3ኛ ደረጃ ላይ መቀመጥ ችለዋል፡፡
ምድብ ሀ
[table id=232 /]
[league_table 18073]
ምድብ ለ
[table id=242 /]
[league_table 18083]