የአሰልጣኞች አስተያየት | ሲዳማ ቡና 3-1 ኢትዮጵያ ቡና

በ20ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ሲዳማ ቡና ኢትዮጵያ ቡናን 3-1 በማሸነፍ የሊጉን መሪነት ተረክቧል፡፡ ከጨዋታው በኋላ የሁለቱ ክለብ አስልጣኞች በሚከተለው መልኩ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

አሰልጣኝ አለማየው አባይነህ – ሲዳማ ቡና

ስለጨዋታው

በጨዋታው ሙሉ ክፍለጊዜ እኛ ከተጋጣሚያችን የተሻልን ነበርን፡፡ በውጤቱ ደስ ብሎኛል፡፡ እኔ ይህንን እንደምናሳካ እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ ተጫዋቾቼ በጨዋታው በርካታ ኳሶችን አምክነው እንጂ ውጤቱ ከዚህም በላይ መሆን ይችል ነበር፡፡

የሊጉን መሪነት ስለመያዛቸው

የሊጉ መሪ መሆናችን አያዘናጋንም፡፡ የዛሬው ጨዋታ አልፏል፡፡ በሊጉ ገና ቀሪ 10 ጨዋታዎች ይደረጋሉ፡፡በቀጣይ የምናደርጋቸው ጨዋታዎች ላይ ትኩረት እናደርጋለን፡፡ በተለይም ከቅዱስ ጊዮርጊስ ላለለብን ጨዋታ መዘጋጀት ግድ ይለናል፡፡ 

አሰልጣኝ ገዛኸኝ ከተማ – ኢትዮጵያ ቡና

ስለ ጨዋታው

በእንቅስቃሴ ረገድ በተወሰነ መልኩ ጥሩ ለመሆን ሞክረን ነበር፡፡ ነገር ግን ከጨዋታ ውጭ የሆነ እንቅስቃሴ ማድረጋችን ጎድቶናል፡፡ ያም ለመሸነፋችን ምክንያት ነበር ማለት ያስችለናል፡፡ ዛሬ ችግራችን ወደ ፊት መሄድ ነው፡፡  ማመን ያለብን ስህተት ስትሰራ ስህተትን በፀጋ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ ውጤቱንም በፀጋ ተቀብየዋለሁ፡፡ በቀጣይ ጨዋታዎቻችን ችግሮቻችንን ቀርፈን እንቀርባለን፡፡

ስለ አቡበከር ነስሩ

በጨዋታው ላይ ግብ ያስቆጠረልን አቡበከር ታዳጊ ነው፡፡ ቡና ታዳጊዎችን ማፍራት አላማው ነው፡፡ በመጀመሪያ ጨዋታው ይህን አይነት እንቅስቃሴ ማድረጉ ጥሩ የሚባል ነው፡፡

የጋቶች እና አስቻለው አለመኖር

የጋቶች እና አስቻለው ያለመኖር አልጎዳንም፡፡ ቡና ከዚህ ቀደም አስቻለውንም ሆነ ጋቶችን ሳይዝ አሸንፏል፡፡ በቡና ቤት አንዱ ቢወጣ የሚተካው ብዙ ነው፡፡ ያ ለሽንፈታችን ምክንያት ሊሆን አይችልም፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *