ወደ 2017 የካፍ ኮንፌድሬሽን ዋንጫ ምድብ ለመግባት የሚደረጉ የመጨረሻ ዙር የማጣሪያ ጨዋታዎች በ32 ቡድኖች መካከል በሳምንቱ መጨረሻ ቀናት በተለያዩ የአፍሪካ ከተሞች ይደረጋሉ፡፡
ካፍ ሊበርቪል ላይ ቅዳሜ ለሚደረግ ጨዋታ ኢትዮጵያዊንያን ዳኞችን መርጧል፡፡ የጋቦኑ ሲኤፍ ሞናና ከኮትዲቯሩ አሴክ ሚሞሳስ በስታደ አሚቴ የሚያደርጉትን ጨዋታ ኢትዮጵያዊው የፊፋ ኢንተርናሽናል የመሃል ዳኛ ባምላክ ተሰማ እና ረዳቶቹ ሃይለራጉኤል ወልዳይ እና በላቸው ይታየው እንዲመሩ ተመርጠዋል፡፡ ሲኤፍ ሞናና ከቻምፒየንስ ሊጉ በሞሮኮው ዋይዳድ ካዛብላንካ በመለያ ምት ተሸንፎ ወደ ኮንፌድሬሽን ዋንጫው ወርዷል፡፡ አሴክ በበኩሉ በኮንፌድሬሽን ዋንጫ የዘንድሮውን አመት ውድድር እየተካፈለ ይገኛል፡፡
ባምላክ ከዚህ ቀደም በቻማፒየንስ ሊግ ጨዋታ ሶስ ላይ ኤቷል ደ ሳህል የኮትዲቯሩን ኤኤስ ታንዳን ያሸነፈበትን ጨዋታ መምራቱ ይታወሳል፡፡ በኮንፌድሬሽን ዋንጫ በዘንድሮው አመት ሁለት ጨዋታዎችን መምራት የቻለው ሃይለየሱስ ባዘዘው መሆኑ ይታወሳል፡፡