የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 27ኛ ሳምንት ዛሬ ፣ ነገ እና ከነገ በስቲያ ይካሄዳሉ፡፡ ሶከር ኢትዮጵያም ከጨዋታዎቹ ጋር በተያያዘ ያሉትን የተጫዋቾች ጉዳት ፣ ቅጣት እንዲሁም ወደ ጨዋታ የሚመለሱ ተጫዋቾችን እንዲህ አጠናቅራለች፡፡
ቅዳሜ ሚያዝያ 28 ቀን 2009
መከላከያ ከ ድሬዳዋ ከተማ (08:30 ፤ አአ ስታድየም)
በ27ኛው ሳምንት የመክፈቻ ጨዋታ መከላከያ ሽመልስ ተገኝን የማያገኝ ሲሆን ድሬዳዋ ከተማ በረከት ሳሙኤልን በጉዳት ምክንያት ሳይዝ ወደ አአ መጥቷል፡፡ ሆኖም የወሳኝ ተጫዋቾቹ ሳምሶን አሰፋ እና ሐብታሙ ወልዴ ከጉዳት ማገገም ለድሬዳዋ የምስራች ሆኗል፡፡
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ ሲዳማ ቡና (10:30 ፤ አአ ስታድየም)
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አማካዩ ቢንያም በላይን ከጉዳት መልስ እንደሚያገኝ ሲጠበቅ ሲዳማ ቡና ተከላካዩ አንተነህ ተስፋዬን በጉዳት የማያሰልፍ ይሆናል፡፡
እሁድ ሚያዝያ 29 ቀን 2009
ደደቢት ከ ፋሲል ከተማ (08:30 ፤ አአ ስታድየም)
ደደቢት ሮበን ኦባማን በጉዳት በዚህ ጨዋታም የማያገኘው ሲሆን ከመከላከያ በተደረገው ጨዋታ በ2 ቢጫ ከሜዳ የወጣው ዳዊት ፍቃዱ በቅጣት አይሰለፍም፡፡
በፋሲል ከተማ በኩል ሰለሞን ገብረመድህን አሁንም ወደ ሜዳ የማይመለስ ሲሆን አብዱራህማን ሙባረክ ወደ ጨዋታ ይመለሳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
አርባምንጭ ከተማ ከ አዳማ ከተማ (09:00 ፤ አርባምንጭ)
አርባምንጭ አንተነህ መሳ ፣ ወንድወሰን ሚልኪያስ እና ተሾመ ታደሰን በጉዳት የሚያጣ ሲሆን በአዳማ በኩል ሲሳይ ቶሊ ፣ ተሰፋዬ በቀለ እና በክለቡ ቅጣት የተጣለበት ሞገስ ታደሰ አይኖሩም፡፡ የሱራፌል ዳኛቸው እና ፋሲካ አስፋው የመሰለፍ ጉዳይም አጠራጣሪ ነው፡፡
ሀዋሳ ከተማ ከ ወልድያ (09:30 ፤ ሀዋሳ)
ሀዋሳ ከተማ ግብ ጠባቂው ሶሆሆ ሜንሳህ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ባደረጉት ጨዋታ ባስተናገደው ጉዳት ከዛሬው ጨዋታ ውጪ ሲሆን በወልድያ በኩል ምንም የጉዳት እነና ቅጣት ዜና የለም፡፡
ጅማ አባ ቡና ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ (09:30 ፤ ጅማ)
በሁለቱም በኩል አዲስ የተመዘገበ የተጫዋች ጉዳት ዜና የሌለ ሲሆን ያለፉትን 3 ተከታታይ ጨዋታዎች ያላደረገው ግብ ጠባቂው ሮበርት ኦዶንካራ ዛሬ ይሰለፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከ ኢትዮጵያ ቡና (10:30 ፤ አአ ስታድየም)
በሁለቱም በኩል አዲስ የተመዘገበ ጉዳት የለም፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ቡና ወሳኝ ተጫዋቾቹ ጋቶች ፓኖም ፣ አብዱልከሪም መሐመድ እና ኤልያስ ማሞ ከጉዳት የተመለሱ ሲሆን ጋቶች እና አብዱልከሪም በዚህ ጨዋታ ላይ ይሰለፋሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ሰኞ ሚያዝያ 30 ቀን 2009
አዲስ አበባ ከተማ ከ ወላይታ ድቻ (10:00 ፤ አአ ስታድየም)
በአዲስ አበባ ከተማ በኩል ዲሜጥሮስ ወልደስላሴ በጉዳት የመሰለፉ ጉዳይ አጠራጣሪ ሲሆን ከሲዳማ ቡና በተደረገው ጨዋታ በሁለት ቢጫ ከሜዳ የወጣው ዳንኤል አባተ በቅጣት የማይሰለፍ ይሆናል፡፡ በጉዳት ላይ የነበሩት አቤል ዘውዱ ፣ ዘሪሁን ብርሀኑ ፣ እንየው ካሳሁን እና ተክለማርያም ሻንቆ ከጉዳታቸው ያገገሙ ሲሆን መሰለፍ አለመሰለፋቸው በእለቱ ይታወቃል ተብሏል፡፡
በወላይታ ድቻ በኩል እስከ አመቱ መጨረሻ ድረስ በጉዳት ከማይኖረው ቶማስ ስምረቱ በቀር አዲስ የተጫዋች ጉዳት የለም፡፡