ካፍ ለአፍሪካ ከ17 አመት በታች ዋንጫ ከኢትዮጵያ አንድ ዳኛ መርጧል

ጋቦን በግንቦት ወር በምታስተናግደው የአፍሪካ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ጨዋታዎችን የሚመሩ ዳኞችን እና ረዳት ዳኞችን ካፍ ይፋ አድርጓል፡፡

በሳምንቱ መጨረሻ እሁድ በሚጀመረው የታዳጊዎች ቻምፒዮና ላይ የሚዳኙ 14 የመሃል ዳኞች እና 15 ረዳት ዳኞች ካፍ መርጧል፡፡ ከነዚህም መካከል ኢትዮጵያዊው ረዳት ዳኛ ተመስገን ሳሙኤል በውድድሩ ላይ የሚሳተፍ ብቸኛው ኢትዮጵያዊ ዳኛ ሆኖ በካፍ ተመርጧል፡፡ ተመስገን ከዚህ ቀደም የካፍ ቻምፒየንስ ሊግ፣ ኮንፌድሬሽን ዋንጫ፣ የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ እና የቻን ማጣሪያ ጨዋታዎች በረዳት ዳኛነት የመራ ሲሆን አሁን ላይ ከ17 ዓመት በታች የአፍሪካ ዋንጫ ላይ በዳኝነት የመሳተፍ እድልን አሳክቷል፡፡

ጨዋታዎች የሚመሩ ዳኞች የተመለመሉት ከአልጄሪያ፣ ብሩንዲ፣ ኮትዲቯር፣ ጂቡቲ፣ ዲ.ሪ. ኮንጎ፣ ግብፅ፣ ጋቦን፣ ጋና፣ ኬንያ፣ ማዳጋስካር፣ ናይጄሪያ፣ ሴኔጋል፣ ሶማልያ፣ ቱኒዚያ፣ ቤኒን፣ ቡርኪናፋሶ፣ ኮሞሮስ፣ ጊኒ፣ ሌሶቶ፣ ሊቢያ፣ ሞሮኮ፣ ኢትዮጵያ፣ ሞዛምቢክ፣ ኒጀር፣ ሲሸልስ እና ታንዛኒያ ናቸው፡፡

በስምንት ሃገራት መካከል የሚደረገው ውድድር አዘጋጇን ጋቦን ጨምሮ፣ ካሜሮን፣ ጋና፣ ጊኒ፣ ማሊ፣ ታንዛኒያ፣ ኒጀር እና አንጎላ ይሳተፋሉ፡፡ በመክፈቻው ጋቦን ጊኒን ስትገጥም፣ ካሜሮን ከጋና የእለቱ ሁለተኛ ጨዋታ ነው፡፡ በምድብ ሁለት ሰኞ የወቅቱ ቻምፒዮን ማሊ ከታንዛኒያ እንዲሁም አንጎላ ከኒጀር ይፋለማሉ፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *