ኢትዮጵያ ቡና በ3 ተጫዋቾቹ ላይ የዲሲፕሊን ቅጣት ማስተላለፉ ታውቋል፡፡ ተከላካዩ አህመድ ረሺድ የአንድ ወር ደሞዙን ሲቀጣ በቀጣይ ጨዋታዎች እና የልምምድ መርሀግብሮች ላይ እንዳይገኝ እግድ ተላልፎበታል፡፡ ዮሐንስ በዛብህ እና አስቻለው ግርማ ደግሞ በተመሳሳይ የአንድ ወር ደሞዝ ተቀጥተዋል።
በውሳኔው ዙርያ ለሶከር ኢትዮጵያ አስተያየታቸውን የሰጡት የኢትዮጵያ ቡና ስራ አስኪያጅ አቶ በላይ እርቁ የቅጣቱ ምክንያት ከቡድን ስብሰባ በመቅረታቸው እንደሆነ ገልጸው አህመድ ረሺድ ደግሞ በተደጋጋሚ የማይገኝ በመሆኑ ቅጣቱ ከፍ እንዳለበት ተናግረዋል፡፡
አህመድ ረሺድ በከለሉ ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጠው ምላሽ በሁኔታው እንዳዘነና የተቀነሰበት መንገድ እንዳስገረመው ገልፆ በቤተሰብ ችግር ባለመገኘቱ መቀጣቱንም ተናግሯል፡፡ ” ስብሰባ በመቅረት ምክንያት የተቀጣ በአለም የመጀመርያው ሳልሆን አልቀርም” ሲል መገረሙን ገልጿል፡፡
በትላንትናው እለት የአሰልጣኝ ለውጥ ያደረገው ኢትዮጵያ ቡና የቅጣት ውሳኔ እና የአሰልጣኝ ለውጡ በደጋፊው ላይ ስለሚያስነሳው ቅሬታ አስተያየታቸውን የሰጡት ስራ አስኪያጁ አቶ በላይ ” ሁሉንም ማስደሰት አይቻልም ሁሌም የምታስቀድመው የቡድን ህልውና ላይ ነው። አሁን ቡድኑ ላይ ለውጥ ሊመጣ አልቻለም፡፡ ያሉትን ነገሮች ለማስተካከል ውሳኔዎች ያስፈልጋሉ። ክለቡ ወደ ፊት መድረስ የሚፈልገው ግብ አለ፡፡ እዛም ለማድረስ ጠንክረን እየሰራን እንገኛለን” በማለት ተናግረዋል።