አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን 29 ተጫዋቾችን ስብስብ ይፋ ሲያደርጉ በዝርዝር ውስጥ አለመካተቱ መነጋገርያ ከሆኑት ተጫዋቾች አንዱ ፍሬው ሰለሞን ነው፡፡
በሀዋሳ ከተማ የመጀመርያ የውድድር ዘመን ቆይታው ሰኬታማ ጊዜ እያሳለፈ የሚገኘው ፍሬው ከሶከር ኢትዮጵያ ጋር ባደረገው ቆይታ በብሄራዊ ቡድን ምርጫ ውስጥ አለመካተቱ እንዳስከፋው ገልጿል፡፡ ” ጥሩ ጊዜ እያሳለፍኩ ባለሁበት ወቅት ለብሔራዊ ቡድን ካልተጫወትኩ መቼ ልጫወት ነው? በዚህ ሁኔታ አለመመረጤ ቢያስከፍኝም እንደ ሌላው ቀን ብዙ አልከፋኝም፡፡ ምክንያቱም አሁን ያለሁበትን አቋም የስፖርት ቤተሰቡ በአጠቃላይ ሁሉም በግልፅ የሚያየው እና የሚያምነው ጉዳይ ስለሆነ ለብሔራዊ ቡድን አለመጠራቴ ብዙ አልተከፋውም፡፡ ስለ እኔ ህዝቡ ይመስክር ብዬ ትቼዋለው” ብሏል፡፡
ሀዋሳ ከተማ በ27ኛው ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ወልድያን 2-1 ባሸነፈበት ጨዋታ ላይ ፍሬው ግብ በማስቆጠር እና ለግብ አመቻችቶ በማቀበል ከፍተኛውን ሚና መወጣት ችሏል፡፡ ከአማካይ ቦታ እየተነሳ በሊጉ ያስቆጠራቸውን ጎሎች መጠን ወደ 10 ከፍ በማድረግም ቀዳሚው የአማካይ ስፍራ ተጫዋች ሆኗል፡፡
ፍሬው ለዚህ የግብ ማስቆጠር ብቃቱ መሻሻል የቡድኑ እንቅስቃሴ ምክንያት እንደሆነ ያምናል” ቡድኑ የሚከተለው የአጨዋወት ዘይቤ ጎል ለማስቆጠር ምቹ ነው። አብዝቶ በማጥቃት ስለሚጫወት ነው በርካታ ጎል ላስቆጥር የቻልኩት፡፡ ይህ ደግሞ ለእኔ የምፈልገው አጨዋወት በመሆኑ በጣም ተመችቶኛል። ለዛ ነው ጎል ማስቆጠርም ሆነ ጥሩ ጊዜ እንዳሳልፍ የረዳኝ፡፡”
ፍሬው በመጨረሻም በሀዋሳ ከተማ የውድድር ዘመን ጉዞ ላይ ያለውን አስተያየት እንዲህ ባለ መልኩ አስቀምጧል፡፡
” በአንደኛው ዙር በሜዳም ሆነ ከሜዳ ውጪ ብዙ ችግሮች ነበሩብን፡፡ ከሜዳ ውጭ የነበረብንን ክፍተት በሚገባ ቀርፈን አስተካክለናል። ሜዳ ውስጥ የነበረብንን ክፍተትም ከአንደኛው ዙር ሁለተኛው ዙር ላይ አስተካክለናል። ሙሉ ለሙሉ በማጥቃት ላይ አተኩረን ኳስ እንይዛለን፡፡ በዚህ እንቅስቃሴ ውስጥ ኳስ ከተነጠቅን በመልሶ ማጥቃት ተከላካዮቻችንን እናጋልጥ ነበር። ሁለተኛው ዙር ይህን ክፍተታችንን በመድፈን ጥሩ መሻሻል ብናሳይም አሁን መጨረሻ ላይ ግን መዳከሞች ታይተውብናል።”