ካሜሩን በ2019 ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የሚደረጉ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታዎች አርብ ተጀምረዋል፡፡ በምድብ 6 ከጎረቤት ኬንያ ከምዕራብ አፍሪካዊያኑ ሴራሊዮን እና ጋና ጋር የተደለደለው ኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የመጀመሪያ ጨዋታውን ኩማሲ ላይ ከምድቡ ሰፊ የማለፍ እድል እንዳላት የተነገረላትን ጋናን ይገጥማል፡፡ ዋሊያዎቹ ሀሙስ ጠዋት ወደ ኩማሲ ያቀኑ ሲሆን አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ስለቡድኑ ዝግጅት፣ ስለተጋጣሚ ሃገር ጋና፣ ከጨዋታው ስለተቀነሱ ተጫዋቾች እና መሰል ጉዳዮችን ለሶከር ኢትዮጵያ የሰጡትን አስተያየት እዲሁ አቅርበነዋል፡፡
በዩጋንዳው የአቋም መለኪያ ጨዋታ በሁለቱም ግማሾች ሁለት ብድኖችን ስለማሰለፋቸው
“ክፍተቶችን ሙሉ ለሙሉ ለማየት አንድን ቡድን በ45 ደቂቃ መገምገም ከባድ ነው፡፡ በ45 ደቂቃ እንቅስቃሴ 90 ደቂቃ የመጫወት አቅም አለው ብለን ለመደምደም የዩጋንዳው ጨዋታ አላስቻለንም፡፡ ቢሆንም 45 ደቂቃ ማጫወቱ የተሻለ ነው፡፡ እንዲሁም ከዜሮ አንድ ይሻላል፡፡ ያሉትን ልጆች አሳትፈን ለማየት ሞክረናል፡፡ ያሉትን ምን ጥሩ ነገሮች እንዲሁም ምን እንደሚጎለን ይህ ጨዋታ አሳይቶናል፡፡”
በግራ መስመር ተከላካይ ቦታ ተፈጥሮአዊ የግራ እግር ተጫዋቾች ቡድኑ አለመያዙ
“ግራ እግር ችግር አለ ሃገራችን ውስጥ፡፡ በቦታው አሉ የምትላቸው ተጫዋቾች አንዱ ተስፋዬ በቀለ ከእዛ ውጪ አበባው ብታቆ ነው፡፡ ከእነዚህ ውጪ አሉ የምትላቸው ልጆች ጥሩ ቢሆኑም ግዜ የሚፈልጉ ተጫዋቾች ናቸው፡፡ ለምሳሌ የፋሲል ከተማ አምሳሉ ጥላሁን ጥሩ ተጫዋች ነው፡፡ ግን የታክቲክ ዲስፕሊን ላይ ግዜ ይፈጅበሃል፡፡ ወደፊት ትልቅ ተጫዋች እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ፡፡ በሃዋሳ ከተማ ውስጥም የሚጫወት ጥሩ ልጅ (ደስታ ዮሃንስ) አለ፡፡ እሱም በጉዳት ረጅም ግዜ ከሜዳ የራቀው፡፡ ስለዚህ እሱ ቢኖር ቦታው መሸነፈን ይቻል ነበር፡፡ ቦታውን ይሸንፍናል ብለን የምናስበው በቦታው እየተጠቀምን ነው ያለነው፡፡”
ስለጋና እና እሁድ ስለሚካሄደው ጨዋታ
“ጋና በአለማችን አሉ ከሚባሉት ምርጥ ቡድኖች መካከል አንዱ ነው፡፡ ጋና የት ነው ያለው ብለን ስናይ እና እያንዳንዱ ተጫዋቾቻችንን በንፅፅር ስናስቀምጥ ያለን ልዩነት ብዙዎቻችን የምንረዳው ነው፡፡ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የሚፈልገው አንደኛ መሆን ነው የደም ጉዳይ ሆኖ ሁለተኝ መሆን አይፈልግም፡፡ መሸነፍ ባህላችን አይደለም፡፡ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ የሚፈልገው ማሸነፍን ነው፡፡ ለማሸነፍ ነው ደግሞ ቅድሚ መሰራት ያለባቸው ተጓዳኝ ስራዎች በጣም አስፈላጊ ናቸው፡፡ የወዳጅነት ጨዋታዎችም ጋናን የመሰለ ጠንካራ ቡድን ጋር ከመጫወትህ በፊት ማካሄድ አለብህ፡፡ ጋና ጠንካራ ቡድን ነው፡፡ እኔም ከተጫዋቾቼ ጋር በመሆን የጋናን እንቅስቃሴ አብረን አይተናል፡፡ የዩጋንዳው አሰልጣኝ ሚቾም ስለጋና ያለውን ልምድ እና እውቀት አካፍሎናል፡፡ አንድ ሙያተኛ ብቻውን መስራት የሚችለው ነገር የለም፡፡ ስለዚህም ስለጨዋታው ከሚቾ ጋር ያደረግነው ውይይት በጣም መልካም ነው፡፡ ስለጋና ጥሩ ፍንጭ ሰጥቶኛል፡፡”
የናትናኤል ዘለቀ እና ምንተስኖት አዳነ መቅረት የሳላዲን ባርጌቾ ወደ ቡድን መቀላቀል
“ወቅታዊ ብቃት ወሳኝ ነው፡፡ የመጀመሪያ ምርጫው ሲካሄድ ሳላዲን ባርጌቾ በተከላካይ መስመር የነበረው በራስ መተማመኑ ከፍተኛ ስለነበር የሚፈጥራቸው ስህተቶች ቡድኑን ዋጋ የሚያስከፍሉ ነበሩ፡፡ በዚህ ምክንያት አልተጠራም ነበር፡፡ አሁን ደግሞ ዘሪሁን ሸንገታም ስላለ የነበረቡትን ስህተቶች ከዘሪሁን ጋር እንዲያርም እንነጋገር ስለነበር እንደበፊቱ አይቀብጥም፡፡ ተከላካይ ማለት የማይቀብጥ ጠንቃቃ የሆነ ነው፡፡ በዚህ መልኩ ለውጥ የሚያሳይ ማንኛውም ተጫዋች ይጠራል፡፡ በሌላ በኩል እነዛ ሁለት ተጫዋቾች ልክ አዲስ አበባ እንደቀሩት አምስቱ ልጆች ከቡድኑ አልተቀነሱም አሁንም አሉ፡፡ ይህንን እንድትረዱልኝ እፈልጋለው፡፡ ቡድኑን ከጋና ሲመልስ የሚቀላቀሉ ነው የሚሆኑት፡፡ ሁለቱ የጊዮርጊስ የተከላካይ አማካይ ተጫዋቾች ውድድር በጣም ነው የበዛባቸው፡፡ ጫና በጣም በዝቶባቸዋል፡፡ ጊዮርጊስ ቻምፒዮን እንዲሆን ትልቁን ሚና የተጫወተው ምንተስኖት አዳነ ነው፡፡ ይህ ልጅ ጉልበቱን መጦ ጨርሷል ስለዚህ ማገገም መቻል አለበት፡፡ የሰው ልጅ ማሽን አይደለም ልትጠበቀው ይገባል፡፡”