የኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ 2ኛ ዙር ጨዋታዋች ዛሬም ቀጥለው ሲውሉ ወልድያና ጅማ አባቡና ተጋጣሚዎቻቸውን በመርታት ወደ ሩብ ፍፃሜ ተቀላቅለዋል ፡፡
08፡30 ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን ከ ወልድያ ያገናኘው ጨዋታ በወልድያ አሸናፊነት ተደምድሟል፡፡ በመጀመሪያው አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች ተመጣጣኝ እንቅስቃሴ ያደረጉ ሲሆን ጥቂት የግብ ሙከራዎች ተስተናግደዋል፡፡ ፒተር ኑዋድኬ እና ቢንያም በላይ በባንክ ፣ አንዱአለም ንጉሴ እና ምንያህል ይመር ያደረጉት ሙከራ ተጠቃሽ ነበር፡፡
በዝናብ የታጀበው የሁለተኛው አጋማሽ ክፍለ ጊዜ እንደመጀመርያው ሁሉ የተቀዛቀዘ መልክ የነበረው ሲሆን ፒተር መልካም የግብ ማስቆጠር አጋጣሚ አግኝቶ በግብ ጠባቂው ቤሊንጌ የከሸፈበት ተጠቃሽ ሙከራ ነበር፡፡
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ያለ ግብ መጠናቀቁን ተከትሎ አሸናፊውን ለመለየት የመለያ ምቶች ያመሩ ሲሆን እያንዳንዳቸው 10 የመለያ ምቶች መትተው ወልድያዎች አንድ ሲያመክኑ ባንክ ሁለት አምክነው ጨዋታው በወልድያ 9-8 አሸናፊነት ተጠናቋል፡፡
የመጀመሪያው ጨዋታ እስኪጠናቀቅ ድረስ በፈጀው ሰአት ምክንያት ከተያዘለት ክፍለ ጊዜ ዘግይቶ የተጀመረው የደደቢት እና የጅማ አባ ቡና ጨዋታ በጅማ አባ ቡና የበላይነት ተጠናቋል፡፡
በኳስ ቁጥጥር የተሻለ የተንቀሳቀሱት ጅማ አባ ቡናዎች በከፊል ዋና ተሰለፊዎች ሳይዝ ወደ ሜዳ በገባው ደደቢት ላይ ብልጫ መውሰድ ችለዋል፡፡ ከዕረፍት በፊት አሜ መሀመድ እና ሄኖክ ኢሳያስ ያደረጓቸው ጥሩ ሙከራዎችም የሚጠቀሱ ናቸው፡፡
ከዕረፍት መልስ ጅማዎች በቀኝ መስመር በኩል አመዝነው ጫና ፈእረው ሲጫወቱ በ54ኛው ደቂቃ ከብሔራዊ ቡድነኑ የጋና ጉዞ የተቀነሰው አሜ መሀመድ አባ ቡና አሸናፊ የሆነበትን ብቸኛ ጎል አስቆጥሯል፡፡
የዛሬ ውጤቶችን ተከትሎ ወልድያ እና ጅማ አባ ቡና ወደ ሩብ ፍጻሜው በማለፍ ትላንት ተጋጣሚዎቻቸውን ያሸነፉት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና መከላከያን ሲቀላቀሉ ነገ አርባምንጭ ከተማ ከ ወላይታ ድቻ ፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከ ኢትዮጵያ ቡና በሚያደርጉት ጨዋታ ተጨማሪ ሩብ ፍጻሜውን የሚቀላቀሉ ቡድኖች የሚለዩ ይሆናል፡፡