የኢትዮጵያ ጥሎ ማለፍ 2ኛ ዙር ዛሬ በተደረገ አንድ ጨዋታ ሲቀጥል አዲስ አበባ ከተማ ሲዳማ ቡናን 1-0 በማሸነፍ ወደ ሩብ ፍጻሜው የተሸጋገረ 7ኛው ክለብ መሆን ችሏል፡፡
አዲስ አበባ ከተማ የጨዋታውን ብቸኛ የድል ግብ ያገኘው ገና ጨዋታው እንደተጀመረ ነበር፡፡ በ2ኛው ደቂቃ ከመሰመር የተሻገረውን ኳስ አጥቂው ፍቃዱ አለሙ ወደ ግብነት ቀይሯል፡፡
በውድድር ዘመኑ በቋሚነት ከተሰለፉ ተጫዋቾች መካከል ጥቂቶቹ ላይ ለውጥ በማድረግ ወደ ሜዳ የገባው ሲዳማ ቡና የአቻነች ጎል ለማስቆጠር ጫና ፈጥሮ መንቀሳቀስ ቢችልም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በተለይ በመጀመርያው አጋማሽ የመጨረሻ ደቂቃዎች የፈጠሯቸውን የጎል እድሎች በዳንኤል ተሾመ ጥረት ጎል ሳይሆኑ ቀርተዋል፡፡
ድሉን ተከትሎ ከፕሪምየር ሊጉ መውረዱን ያረጋገጠው አዲስ አበባ ከተማ ወደ ሩብ ፍጻሜ መሸጋገር የቻለ ሲሆን ረቡዕ 10:30 ላይ አዳማ ከተማ ከ ፋሲል ከተማ በሚያደርጉት ጨዋታ ወደ ሩብ ፍጻሜው የሚያልፈው የመጨረሻ ቡድን የሚለይ ይሆናል፡፡
የሩብ ፍጻሜ መርሀ ግብር
ማክሰኞ ሰኔ 20 ቀን 2009
10:30 ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ መከላከያ
ረቡዕ ሰኔ 21 ቀን 2009
10:30 ወልድያ ከ ፋሲል ከተማ/አዳማ ከተማ
ሀሙስ ሰኔ 22 ቀን 2009
08:30 ጅማ አባ ቡና ከ አአ ከተማ
10:30 ወላይታ ድቻ ከ ኢትዮ ኤሌክትሪክ