በኢትዮዽያ ከፍተኛ ሊግ በምድብ ሀ 29ኛ ሳምንት ትላንት በአዲስ አበባ ስታድየም በሱሉልታ እና በመቀለ ከተማ መከከል በተደረገ ጨዋታ 69ኛው ደቂቃ ላይ በመቀለ ከተማ 1-0 መሪነት እየተከነወነ በነበረው ጨዋታ የዕለቱ ዳኛ አወዛጋቢና አጨቃጫቂ ውሳኔ በሰጡት ፍፁም ቅጣት ምት ምክንያት የሱሉልታ ከነማ ተጨዋቾች ተበሳጭተው ጨዋታውን አቋርጠው መውጣታቸው ይታወቃል። አመሻሽ ላይም የእለቱ ዳኛ ደረጄ ገብሬምየአንድ አመት ቅጣት እንደተላለፈባቸው መዘገባችን ይታወሳል፡፡
የኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን በትላንትናው እለት ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ ለተፈጠረው የቴክኒክ ስህተት እና ለተቋረጠው ጨዋታ ጥፋተኛ ነው በሚል የዕለቱ ዳኛ ፌዴራል ዳኛ ደረጄ ገብሬ ላይ ለአንድ አመት ጨዋታውን እንዳያጫውት ሲቀጣው ማክሰኞ ሊካሄድ በነበረው ጨዋታ ላይ የዕለቱ ኮሚሽነር በመሆን ተመድበው በረቡዕ ጨዋታ ላይ የተቀየሩት እና ትላናት በተቋረጠው ጨዋታ ላይ ምንም አይነት ተሳትፎ ያልነበራቸውን አቶ ይግዛው ብዙን በተመሳሳይ ለአንድ አመት ቀጥቷል፡፡ አቶ ይግዛው የተቀጡበትን ገዳይ ፌዴሬሽኑ በይፋ ያልገለፀ ሲሆን ለማጣራት ያደረግነው ጥረትም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
በአጠቃላይ በዘንድሮ አመት ውድድሮች ላይ በዳኞች ብሔራዊ ኮሚቴ የተከናወኑ መልካም ስራዎች እንዳሉ ሁሉ የኮሚቴውን የስራ እንቅስቃሴ ላይ ጥያቄ የሚያስነሱ ተግባራት መከናወናቸው የሚታወቅ ነው ። ለአብነት ያህል ከዳኞች እና ኮሚሽነር ምደባ ጋር ተያይዞ የዳኞች ብሔራዊ ኮሚቴ የተወሰኑ ዳኞችን እና ኮሚሽነሮችን ብቻ ደጋግሞ መመደብ ፣ እንደ ጨዋታው ክብደት እና አስፈላጊነት ጨዋታውን በብቃት የሚመሩ ዳኞች እና ኮምሽነሮችን አለመመደብ ፣ አንድ ዳኛ የአንድ ክለብ በርካታ ጨዋታዎችን እንዲዳኝ ማደርግ ፣ ጨዋታን እንዲያጫውቱ ከአራት ቀን በፊት መመደባቸው ተነግሯቸው ክልልም ከሆነ በተለያየ ስፍራ ጨዋታውን ሊመሩ ጉዞ ከጀመሩ በኋላ ጨዋታው ሊደረግ ሰአታት ሲቀረው ዳኞችን መቀየር ፣ የዳኞች ብሔራዊ ኮሚቴ ሜዳ ስህተት የሰሩ ዳኞች ላይ አስፈላጊውን ቅጣት ከወሰነ በኋላ ውሳኔው የማይፀናበት መንገድ ፣ ክለቦች እከሌ ዳኛ አያጫውተን ብለው የሚያቀርቡትን ጥያቄ ተቀብሎ ዳኞች ጥያቄ ያቀረቡትን ክለቦች እንዳያጫውቱ ማድረግ በዋናነት በዘንድሮ ውድድር አመት የተመለከትናቸው ክፍተቶች ሲሆኑ በዚህ ጉዳይ ላይ የፌዴሬሽን የዳኞች ብሔራዊ ኮሚቴ የሚሰጠው ምላሽ ካለ የምናስተናግድ መሆናችን ለመግለፅ እንወዳለን።