የኢትዮጵያ አንደኛው ሊግ የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች ትላንት ሲካሀሄዱ ወደ ከፍተኛ ሊግ ያደጉት 6 ቡድኖች ተለይተው ታውቀዋል፡፡ ከ5 ምድቦች አንደኛ ደረጃ ይዘው ያጠናቀቁት ክለቦች በቀጥታ ከፍተኛ ሊጉን ሲቀላቀሉ አንድ ቡድን በጥሩ ሁለተኝነት ከፍተኛ ሊጉን መቀላቀል ችሏል፡፡
ምድብ ሀ
የምዕራብ ኢትዮጵያ ክለቦች በሚሳተፉበት ምድብ ሀ መሪው ሚዛን አማን በሜዳው ጋምቤላ ዩኒቲን አስተናግዶ 3-0 አሸንፎ ከፍኛ ሊጉን መቀላቀል ችሏል፡፡ በዚሁ ምድብ የማለፍ እድሉ በሚዛን አማን ነጥብ መጣል ላይ ተንጠልጥሎ የነበረው ቱሉ ቦሎ ሆለታ ከተማን 5-1 ማሸነፍ ቢችልም የማለፍ ህልሙ በሚዛን አማን ማሸነፍ ምክንያት ሳይሳካ ቀርቷል፡፡
ምድብ ለ
በምስራቁ የሀገሪቱ ክፍል የሚገኙ ክለቦችን ያካተተውን ምድብ በ38 ነጥብ እየመራ ወደ ሐረር የተጓዘዌ መቂ ከተማ ሐረር አባድርን 3-0 በማሸነፍ ከፍተኛ ሊጉን ተቀላቅሏል፡፡ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የነበረው ሞጆ ከተማ በተመሳሳይ ወደ ሐረር ተጉዞ ሐረር ሲቲን 1-0 ፣ 3ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ባቱ ከተማም ካሊ ጅግጅጋን 7-3 ቢረቱም የከፍተኛ ሊጉን ትኬት ሳይቆርጡ ቀርተዋል፡፡
ምድብ ሐ
የሰሜን ኢትዮጵያ ቡድኖች በሚገኙበት በዚህ ምድብ አመቱን በመሪነት የዘለቀው ደሴ ከተማ ወደ እንጅባራ አቅንቶ አዊ አምፒልታቅን 2-1 ሲያሸንፍ ተከታዩ ዳባት ከተማ በአምባ ጊዮርጊስ በመሸነፉ ደሴ ከተማ አንድ ሳምንት በሚቀረው ምድብ አስቀድሞ ማለፉን ማረጋገጥ ችሏል፡፡
ምድብ መ
በመካከለኛው የኢትዮጵያ ክፍል የሚገኙ ክለቦች የተደለደሉበትን ምድብ ሀ የካ ክፍለ ከተማ ከአንድ ሳምንት ቀደም ብሎ ወደ ከፍተኛ ሊግ መግባቱን ሲያረጋግጥ በትላንትናው እለት አዲስ ከተማን የገጠመው ንፋስ ስልክ ላፍቶ 1-0 በማሸነፍ ነጥቡን 43 ቢያደርስም በአምበሪቾ በግብ ልዩነት ተበልጦ በጥሩ ሁለተኝነት ሳያልፍ ቀርቷል፡፡
ምድብ ሠ
የደቡባዊ የሀገሪቱ ክፍል ላይ የሚገኙ ክለቦችን ያሳተፈው ምድብ ላይ አቻ ውጤት ወደ ከፍተኛ ሊግ ለማለፍ በቂው የነበረው ቡታጅራ ከተማ ከ ጎፋ ባሪንቼ አቻ ተለያይቶ ማደጉን ሲያረጋግጥ አምበሪቾ ኮንሶ ኒውዮርክን 3-0 በማሸነፍ በጥሩ ሁለተኝነት ማለፉን አረጋግጧል፡፡
ወደ ከፍተኛ ሊግ ያለፉ ክለቦች
1 ሚዛን አማን
2 መቂ ከተማ
3 ደሴ ከተማ (ፎቶ)
4 የካ ክፍለከተማ
5 ቡታጅራ ከተማ
6 አምበሪቾ