ከ3 ወራት በፊት ከመብራት ኃይል አሰልጣኝነታቸው ተነስተው ኋላ ላይ የተመለሱት ዮርዳን ስቶይኮቭ ለተጨማሪ 2 የውድድር ዘመናት በቀዮቹ ቤት ለመቆየት መስማማታቸውን ፕላኔት ስፖርት ዘግቧል፡፡
አሰልጣኝ ዮርዳን ከ2003 የውድድር ዘመን ጀምሮ በመብራት ሃይል የቆዩ ሲሆን አዲሱ ኮንትራታቸው በ2008 ሲያበቃ በኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ታሪክ ከውጭ አሰልጣኞች በርካታ አመታት በመቆየት የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ አሰልጣኝ ሚቾን ሪከርድ ይሰብራሉ፡፡
ቡልጋርያዊው አሰልጣኝ ለቀጣዩ የውድድር ዘመን የሚያገለግሉ አዳዲስ ተጫዋቾችን ለመመልመል በባህርዳር የሚገኙ ሲሆን የቀድሞ ተጫዋቾቻቸውን መልሰው ለማስፈረም እንቅስቃሴ መጀመራቸው እየተነገረ ነው፡፡ በቅዱስ ጊዮርጊስ የመብራት ኃይል ብቃቱን መድገም የተሳነው ሳሙኤል ሳኑሚ እና በአሰልጣኙ ስር መልካም ዘመናትን ያሳለፈው የንግድ ባንኩ ፊሊፕ ዳውዚን ወደ ክለቡ ለመመለስ ቀዮቹ ፍላጎት አላቸው፡፡
በተያያዘ የመብራት ኃይሉ ወሳኝ አጥቂ በረከት ይስሃቅ ደደቢትን ለመቀላቀል ጫፍ መድረሱ ተወርቷል፡፡ በረከት የመብራት ኃይል ውሉ በዚህ አመት የተጠናቀቀ ሲሆን በበርካታ ክለቦች እይታ ውስጥ ወድቆ ቆይቷል፡፡