የኢትዮጵያ ዋንጫ አሸናፊ ከጥቅምት 2011 በፊት መታወቅ ይኖርበታል

የኢትዮጵያ ዋንጫ በአዲሱ የካፍ ፎርማት ምክንያት ከጥቅምት በፊት መጠናቀቅ እንደሚኖርበት ተገለፀ። 

የአፍሪካ እግርኳስ ኮንፌድሬሽን (ካፍ) ለአባል ሃገራት ፌደሬሽኖች እና እግርኳስ ማህበራት በመጪው አመት በቻምፒየንስ ሊጉ እና ኮንፌድሽን ዋንጫ የሚሳተፉ ክለቦችን እስከጥቅምት ወር እንዲያሳውቁ መመሪያ የሰጠ ሲሆን በኮፍ ኮንፌድሬሽን ዋንጫ ላይ የሚሳተፈውን ክለብ ለመየት የሚያስችለው የኢትዮጵያ ዋንጫ ደግሞ መካሄድ ከነበረበት ዓመት ተጓቶ ለ2011 መዛወሩ ይታወቃል፡፡

ካፍ በአፍሪካ የክለቦች ውድድሮች ላይ ተሳታፊ የሚሆኑ ክለቦችን ዝርዝር እስከጥቅምት 5 እንዲያሳውቁት ለአባል ፌድሬሽኖች እና የእግርኳስ ማህበራት አስታውቋል፡፡ ይህም የኢትዮጵያ ዋንጫ ከጥቅምት መጀመሪያ አስቀድሞ እንዲጠናቀቅ የሚስገድድ ነው፡፡

ጅማ አባ ጅፋር በቻምፒየንስ ሊጉ በታሪኩ ለመጀመሪያ ጊዜ የሚሳተፍ ክለብ ነው፡፡ ካፍ የውድድር ጊዜውን ከመስከረም-ግንቦት ባሉት ወራት ከቀጣዩ አመት ጀምሮ የሚለውጥ ሲሆን ይህንን ተከትሎም በፕሮግራም መዛባት በፍጥነት መጠናቀቅ ከሚገባው ጊዜ ዘግይቶ የሚጨረሱትን ውድድሮች በጊዜ እንዲያጠናቅቅ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌደሬሽን ላይ ጫና ይፈጥራል፡፡