ደቡብ ፖሊስ የመጀመርያ ተጫዋቹን ሲያስፈርም የሁለት ተጫዋቾችን ውል አድሷል

የከፍተኛ ሊግ የበላይ በመሆን ወደ ፕሪምየር ሊግ ያደገው ደቡብ ፖሊስ በዝውውር መስኮቱ የመጀመርያ ዝውውሩን ማከናወኑን ክለቡ ለሶከር ኢትዮጵያ ገልጿል። 

መክብብ ደገፉ ወደ ደቡብ ፖሊስ ያመራ ተጫዋች ነው። ግብ ጠባቂው መክብብ የውድድር ዓመቱን በሀምበሪቾ ያሳለፈ ሲሆን በ2006 ከወላይታ ድቻ ጋር ወደ ፕሪምየር ሊግ በማደግ በተለይ የመጀመርያው ዓመት ላይ ጥሩ ጊዜ ማሳለፍ ችሎ ነበር። መክብብ ከወላይታ ድቻ ከለቀቀ በኋላ በሀዋሳ ከተማ እና አዳማ ከተማ ያልተሳኩ ጊዜያትን ካሳለፈ በኋላ ነበር ወደ ሀምበሪቾ ያመራው። ደቡብ ፖሊስ መክብብን በአንድ ዓመት ውል ያስፈረመው ሲሆን ወደ ወላይታ ድቻ ያመራው መኳንንት አሸናፊን ክፍተት እንደሚሸፍን ታምኖበታል።

ደቡብ ፖሊስ የሁለት ተጫዋቾችንም ውል አድሷል። ክለቡ ወደ ፕሪምየር ሊግ እንዲያድግ ከረዱ ተጫዋቾች መካከል የሚጠቀሱት ብርሀኑ በቀለ እና ሙህዲን ዐብደላ ውላቸው ለተጨማሪ አንድ ዓመት የታደሰላቸው ተጫዋቾች ናቸው።