ፌዴሬሽኑ ከኢትዮጵያ ቡና ጋር ውይይት ሊያደርግ ነው

ኢትዮጵያ ቡና በትኬት ሽያጭ ገቢ ላቀረበው ጥያቄ ፌዴሬሽኑ ምላሽ  ለመስጠት ቀጠሮ ይዟል።

ኢትዮጵያ ቡና ስፖርት ክለብ የ2010 የአዲስ አበባ ስታድየም ገቢ ድርሻ እንዲሰጠው እና የዘንድሮው የውድድር ዘመን የስታድየም ትኬት ሽያጭ በክለቡ አማካኝነት እንዲከናወን ፤ ይህ በአስቸኳይ ካልተፈጸመም ውድድር እንደማያደርግ የሚገልጽ ደብዳቤ ለፌዴሬሽኑ ማስገባቱን በዛሬው ዕለት ይፋ ማድረጉ ይታወቃል።

ደብዳቤውን የተመለከተው የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽንም በጉዳዩ ዙርያ ምላሽ  ለመስጠት  ‹‹ነገ 10:00 ተገናኝተን እንወያይ›› ሲል ለኢትዮዽያ ቡና የቦርድ አመራሮች ቀጠሮ ሰጥቷል።

በኢትዮጵያ ቡና በኩል የቦርድ ሰብሳቢው መቶ አለቃ ፍቃደ ማሞ ፣ ም/ል ሰብሳቢ አቶ ይስማሸዋ ሥዩም እና የደጋፊ ማህበሩ ፕሬዝደንት አቶ ክፍሌ አማረ ክለቡን በመወከል ከፌዴሬሽኑ ጋር ውይይት ለማድረግ በተያዘው ቀጠሮ ላይ እንደሚገኙ ለማወቅ ችለናል።

ኢትዮጵያ ቡና በዚህ ጉዳይ በቀዳሚነት ቅሬታውን በይፋ ይግለጽ ያንሳ እንጂ በተመሳሳይ ሁኔታ ሌሎች ክለቦችም ጥያቄ እንዳላቸው በተደጋጋሚ ሲገለጽ ቆይቷል፡፡  ፌዴሬሽኑም ባለፉት  ዓመታት የተፈጠሩ መሰል ስህተቶችን ዘንድሮ ላለመስራት ከፍተኛ ዝግጅት እያደረገ መሆኑን በፕሪምየር ሊግ ዓመታዊ ስብሰባ ወቅት መግለፁ ይታወሳል።