ኢትዮጵያ የምትሳተፍበት ውድድር በአስመራ ሊካሄድ ነው

የኢትዮጵያ እና ኤርትራ ወጣት ብሔራዊ ቡድኖችን የሚያገናኝ ውድድር በቅርቡ አስመራ ላይ ይደረጋል።

“የሰላም እና ወዳጅነት ዋንጫ” በሚል ስያሜ በየካቲት ወር መጀመሪያ ይደረጋል ተብሎ የሚጠበቀው ውድድር የ10 ቀናት እድሜ የሚኖረው ሲሆን የኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ሶማሊያ እና ጅቡቲ ከ20 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድኖችን ያሳትፋል።

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዘዳንት አቶ ኢሳይያስ ጅራን ጨምሮ የቀጠናው የእግርኳስ አመራሮች ከሳምንት በፊት በአስመራ በነበራቸው ስብሰባ ውድድሩ በሚደረግበት ሂደት ላይ ተነጋግረዋል። የአፍሪካ እግርኳስ ኮንፌዴሬሽን (ካፍ) በበኩሉ 25,000 ዶላር ለኤርትራው ፌዴሬሽን በመስጠት ዝግጅቱን ለማገዝ ተስማምቷል።

የኤርትራ ከ20 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለዚህ ውድድር ከወዲሁ ዝግጅቱን እያደረገ የሚገኝ ሲሆን ዛሬ ኢትዮጵያዊ ዳኞች በሚመሩት የወዳጅነት ጨዋታ የሱዳን አቻውን ያስተናግዳል።

ሁለቱ ሀገራት በቅርቡ ሰላማዊ ግንኙነት ከቀጠሉ በኋላ በብሔራዊ ቡድን እና በክለቦች ደረጃ የወዳጅነት ጨዋታዎችን ለማድረግ ቢታሰብም በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሳካ እንደቀረ ይታወሳል።