የሴካፋ ከ20 ዓመት በታች ዋንጫ መስከረም ላይ ይደረጋል

ዩጋንዳ በቀጣይ ወር የሴካፋ ከ20 ዓመት በታች ዋንጫን ታዘጋጃለች።

በኤርትራ አዘጋጅነት ለመጀመርያ ግዜ ከ 15 ዓመት በታች የሴካፋ ዋንጫ ያካሄደው ሴካፋ አሁን ደግሞ ከሴፕቴምበር 15 ጀምሮ ከ20 ዓመት በታች ውድድር በዩጋንዳ ያካሂዳል። ከዚህ በፊት መሰል የታዳጊ እግር ኳስ ባለማዘጋጀት የሚታማው ሴካፋ በቅርቡ ከብዙዎች ግምት ውጭ በኤርትራ አዘጋጅነት የተሳካ ከ15 ዓመት በታች ውድድር ማካሄዱ ይታወቃል።

ከወራት በፊት ይካሄዳል ተብሎ በተለያዩ ምክንያቶች እስካሁን ድረስ ሳይካሄድ የቆየው ይህ ውድድር አስር ሃገራት ይሳተፉበታል ተብሎ ሲጠበቅ የጅቡቲ መሳተፍ እስካሁን አልተረጋገጠም። እንደነ ዩጋንዳ ፣ ኬንያና ደቡብ ሱዳንን ጨምሮ በርካቶቹ ተወዳዳሪ ሃገራት ዝግጅት የጀመሩ ሲሆን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንም በአሰልጣኝ ዮሴፍ ተስፋዬ መሪነት በዛሬው ዕለት ዝግጅት ጀምሯል።


© ሶከር ኢትዮጵያ