ካፍ በዚህ ሳምንት የኢትዮጵያ ስታዲየሞች የጥራት ደረጃ ይመዝናል

ካፍ ለትግራይ እና ለባህር ዳር ስታዲየሞች የሰጠው ቀነ ገደብ በዛሬው ዕለት ሲጠናቀቅ በድጋሚ ፈቃድ ለማግኘት በቀጣይ ቀናት ይመዘናሉ።

ከወራት በፊት ካፍ ለሁለቱም የኢትዮጵያ ስታዲየሞች አህጉራዊ ጨዋታዎች እንዲያስተናግዱ በሁለት ወራት በቀነ ገደብ ፍቃድ መስጠቱ ይታወሳል፤ በስታዲየሞቹ ሊሟሉ የሚገባቸው ነገሮች በመጥቀስ የሁለት ወራት የተሰጠው ቀነ ገደብም ዛሬ ተጠናቋል። ይህን ተከትሎ የካፍ አባላት በዚህ ሳምንት ስታዲሞሞቹ ያሉበት ወቅታዊ ሁኔታን የሚመዝኑ ሲሆን የባህር ዳር ሐሙስ፣ የትግራይ ስታድየም ደግሞ ከዓርብ በኃላ ባሉት ቀናት በካፍ ሃላፊዎች እንደሚጎበኙ ይጠበቃል።

የካፍ ፍቃድ ካገኘ በኃላ ሁለት ጨዋታዎች ያስተናገደው የትግራይ ስቴድየም በዚህ ሰዓት የሳር ማስተካከል፣ የአጥር፣ የመግቢያ በር እና ሌሎች እድሳቶች እየተደረጉበት ሲገኝ የባህር ዳር ስቴድየም ደግሞ ከባለፈው ይዞታው በተሻለ የድህንነት ካሜራን ጨምሮ በርካታ መሻሻሎች አድርጎ የካፍ ምዘናን እየተጠባበቀ ይገኛል።


© ሶከር ኢትዮጵያ