ደደቢት ሁለት ተጫዋቾች አስፈረመ

በከፍተኛ ሊጉ በርካታ ዝውውሮች ካደረጉት ክለቦች በግንባር ቀደምትነት የሚጠቀሱት ደደቢቶች የቀድሞ ተጫዋቻቸው ዮሐንስ ፀጋይ እና ተከላካዩ እያሱ ለገሰን አስፈርመዋል።

ከዚህ ቀደም በመቐለ፣ ደደቢት፣ ወልቂጤ እና አክሱም የተጫወተው አማካዩ ዮሐንስ ፀጋይ በ2008 እና በ2009 ለሁለት ዓመታት በሰማያዊዎቹ ቤት የተጫወተ ሲሆን በአሁኑ አሰልጣኙ ጌታቸው ዳዊት ስር መቐለ ወደ ፕሪምየር ሊጉ ሲያድግ የጎላ ድርሻ ከነበራቸው ተጫዋች አንዱ ነው። ባለፈው የውድድር ዓመት ከአክሱም ከተማ ጋር ቆይታ የነበረው ተጫዋቹ በተሰጠው የሙከራ ግዜ ክለቡን በማሳመኑ ሲፈርም ከአሰልጣኙ ጋር ለሶስተኛ ጊዜ የሚሰራ ይሆናል።

ሌላው ለደደቢት ፊርማውን ያኖረው ተከላካዩ ኢያሱ ለገሰ ከዚህ በፊት በአዲስ አበባ ከተማ ከሃያ ዓመት በታች ቡድን ቆይታ የነበረው ሲሆን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ታዳጊ ቡድኖችንም አገልግሏል።

መድኃኔ ብርሃኔን ለስሑል ሽረ አሳልፈው የሰጡት ደደቢቶች በከፍተኛ ሊግ እንደሚሳተፉ ከተረጋገጠ በኃላ ጋናዊው አጥቂ ፉሴይኒ ኑሁን ጨምሮ ሌሎች ተጫዋቾችም ይለያያሉ እየተባለ ቢቆይም ተጫዋቾቹ በክለቡ እንደሚቆዩ ለማወቅ ተችሏል።


© ሶከር ኢትዮጵያ