አዳማ ዋንጫ | ፋሲል ከነማ ውድድሩን በድል ጀምሯል

3ኛው የአዳማ ከተማ ዋንጫ ዛሬ ጅማሮውን ሲያደርግ በመክፈቻ ጨዋታ ፋሲል ከነማ ሀዋሳ 3-1 መርታት ችሏል ፤ አዲስ ፈራሚው ኦሴይ ማውሊም ሁለት ግቦችን አስቆጥሯል።

ከዳንኤል ደርቤ በስተቀር በርከት ያሉ ወጣቶችን በመጀመሪያ ተመራጭነት ይዘው የገቡት ሀዋሳ ከተማዎች ገና በ3ኛው ደቂቃ በያሬድ ባየህ ስህተት የተገኘችውን ኳስ ወጣቱ አጥቂ ብሩክ በየነ ለቡድኑም ለውድድሩም የመጀመሪያ የሆነችውን ግብ አስቆጥሯል።

ከግቧ መቆጠር በኃላ ሀዋሳ ከተማዎች በቁጥር በርከት ብለው ወደራሳቸው የግብ ክልል ቀርበው በጥንቃቄ ለመጫወት ምርጫ ማድረጋቸው በጨዋታው የመጀመሪያ 45 ደቂቃ ፋሲሎች ለወሰዱት አንጻራዊ የበላይነት አይነተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል።

ፋሲሎች የተሻሉ በነበሩበት የመጀመሪያ 45 ደቂቃ በተለይ በቀኝ መስመር ተከላካዩ እንየው ካሳሁን በተሰለፈበት በተደጋጋሚ የተጠቀጠቀውን የሀዋሳ የመከላከል አደረጃጀት ለመስበር ከፍተኛ ሚና ሲወጣ ተስተውሏል ምንም እንኳን በተደጋጋሚ በነጻ አቋቋም ኳሶችን ቢያገኝም ደካማ ውሳኔ አሰጣጡ ኳሷቹ ፍሬያማ እንዳይሆኑ አድርጓል።

በ23ኛው ደቂቃ በጥሩ ቅብብል የተገኘውን ኳስ ሙጂብ ቃሲም ከሀዋሳ የግብ ክልል ጠርዝ ላይ አክርሮ በመምታት ቡድኑን አቻ ማድረግ ችሏል። ከግቧ መገኘት በኃላ ይበልጥ የተነቃቁ የሚመስሉት ፋሲሎች በአዲሱ ፈራሚያቸው ኦሲ ማውሊ ከረጅም ርቀት በስቆጠራት ግብ 2-1 እየመሩ ለእረፍት ማምራት ችለዋል።

ከእረፍት መልስ ሀዋሳ ከተማ በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ቀይሮ ለመሞከር ጥረት ሲያደርጉ በአንጻሩ ፋሲሎች ተመሳሳይ ቡድን ይዘው ቀጥለዋል። በ51ኛው ደቂቃም ኦሲ ማውሊ ከእንየው ካሳሁን በግሩም ሁኔታ የተሻማለትን ኳስ ተጠቅሞ ቡድኑን መሪነት ወደ ሦስት ከፍ ያደረገች ጎል ማስቆጠር ችሏል።

በቀሪዎቹ ደቂቃዎች ሁለቱም ቡድኖች ተጨማሪ ግቦችን ለማስቆጠር ተደጋጋሚ ሙከራዎችን ማድረግ ችለዋል በተለይም በ68ኛው ደቂቃ ሙጂብ ለፋሲል እንዲሁም ብርሃኑ በቀለ ለሀዋሳ ያመከኗቸው እጅግ አስቆጪ ሙከራዎች ነበሩ።

ጨዋታው በፋሲሎች የ3-1 የበላይነት መጠናቀቁን ተከትሎ ፋሲል ምድቡን 3 ነጥብና በ2 ንፁህ ግብ መምራት ጀምሯል።


© ሶከር ኢትዮጵያ