ሪፖርት | ወልዋሎ እና ኢትዮጵያ ቡና ነጥብ ተጋርተዋል

በ10ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መቐለ ላይ ወልዋሎ እና ኢትዮጵያ ቡና ያደረጉት ጨዋታ አንድ ለአንድ በሆነ የአቻ ውጤት ተጠናቋል።

ባለ ሜዳዎቹ ወልዋሎዎች ባለፈው ሳምንት በባህር ዳር ሽንፈት ከገጠመው ስብስብ መካከል አብዱልዓዚዝ ኬይታ፣ ፍቃዱ ደነቀ፣ ብሩክ ሰሙ እና ሚካኤል ለማን በማሳረፍ በጃፋር ደሊል፣ ዳዊት ወርቁ፣ ሰመረ ሀፍታይ እና ራምኬል ሎክ ተክተው ወደ ሜዳ ሲገቡ በአንፃሩ ኢትዮጵያ ቡናዎች ከባለፈው ሳምንት ተሰላፊዎቻቸው ምንም ለውጥ ሳያደርጉ ጨዋታውን ጀምረዋል።

ብዙም ሳቢ ባልነበረው የመጀመርያው አጋማሽ የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ወልዋሎዎች ከብዙዎች ግምት ውጭ የተከላካይ ክፍላቸውን ወደ መሐል ሜዳ አስጠግተው ጫና ፈጥረው ለመጫወት ሲሞክሩ ኢትዮጵያ ቡናዎችም ጫናውን ሰብረው በተሳካ ሁኔታ ኳስን ለመመስረት ተቸግረዋል።

በዚህም መጀመርያው አጋማሽ ኢትዮጵያ ቡና ብዙም የግብ ዕድል ያልፈጠሩበት በአንፃሩ ቀጥተኛ ኳስ መርጠው የገቡት ወልዋሎዎች በአጨዋወቱ ብዙ የግብ ሙከራ ያደረጉበት ነበር። የመጀመርያው ሙከራ የነበረውም ጁንያስ ናንጂቡ አክርሮ መቶት ወደ ላይ የወጣው ሙከራ ነበር።

በአጋማሹ በቀጥተኛ አጨዋወት በርካታ ሙከራዎች ያደረጉት ቢጫ ለባሾቹ በሰመረ ሀፍታይ እና ጁንያስ ናንጂቡ ለግብ የቀረቡ ሙከራዎች ያደረጉ ሲሆን በተለይም ሰመረ ሀፍታይ መትቶ ወደ ውጭ የወጣችበት እና በድጋሚ ወጣቱ አጥቂ ከነፃ አቋቋም ላይ ሆኖ መቷት ወንድሜነህ ደረጀ ከግቡ መስመር የመለሳት ወልዋሎን መሪ ለማድረግ የተቃረቡ ነበሩ።

በመጀመርያው አጋማሽ የተጋጣሚን ጫና ተቋቁመው ኳስን ለመንሸራሸር የተቸገሩት ቡናማዎቹ በአጋማሹ በጥሩ የመከላከል ቅርፅ የተጋጣሚን የማጥቅያ መንገድ ቢያከሽፉም ወደ ተጋጣሚ ሜዳ ኳስ ዘልቀው የግብ ዕድል ለመፍጠር ተቸግረዋል። ሆኖም ቡድኑ በጨዋታው የመጀመርያ ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ ወደ ግብነት ልውጦ መሪ መሆን ችሏል። ፍቅረየሱስ ተ/ብርሀን ከሳጥኑ ውጭ አክርሮ በመምታት ግሩም ግብ አስቆጥሮ ቡድኑን መሪ ማድረግ ችሏል።

ቡናዎች ከግቡ በኃላም የተወሰኑ ሙከራዎች አድርገዋል። ከነዚህም እንዳለ ደባልቄ እና ሀብታሙ ታደሰ በተጋጣሚ ሳጥን ውስጥ በጥሩ ቅብብል ለሚክያስ መኮንን ያመቻቹለን ኳስ አማካዩ መትቶ ወደ ውጭ ያወጣው ሙከራ የቡናን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ ማድረግ የሚችል ነበር።

በሁለቱም ቡድኖች በኩል ጥቂት የግብ ሙከራዎች በታየበት ሁለተኛ አጋማሽ ሁለት ቅያሪዎች አድርገው ወደ ሜዳ የተመለሱት ቡናማዎች በአጨዋወት ረገድ ተሻሽለው የታዩበት፤ ወልዋሎዎችም በጣም አስቆጪ ሙከራዎች ያደረጉበት ነበር።

ቡናዎች ከመጀመርያው አጋማሽ በተሻለ የተጋጣሚን ጫና ተቋቁመው የኳስ ቁጥጥር ብልጫ ቢወስዱም በግለ ሰቦች የሚፈጠሩት የቅብብል እና የውሳኔ አሰጣጥ ችግሮች በቡድኑ አጨዋወት እክል ነበሩ። በተለይም ቡድኑ ከመከላከል ወደ ማጥቃት ሲሸጋገር ያለው ዘገምተኛ ሽግግር ተጋጣሚ ወደ መከላከል ቅርፁ እስኪመለስ ጥሩ ፋታ የሰጠ ነበር። በሙሉ የጨዋታው ክፍለ ግየጊዜ በተጠቀሰው ችግር ወደ ግብ ዕድልነት ያልተቀየሩ ጥሩ አጋጣሚዎችም ጥቂት የማይባሉ ነበሩ። በዚህም ቡድኑ በሁለተኛው አጋማሽ የሞከረው ለግብ የቀረበ ሙከራ አልነበረም።

በአንፃሩ የአቻነት ግብ ለማግኘት ተጭነው የተጫወቱት ወልዋሎዎች በርካታ ዕድሎች ፈጥረዋል። ሆኖም በፈቱዲን ጀማል እና ወንድሜነህ ደረጀ ጠንካራ ጥምረት እና በጁንያስ ናንጂቡ ደካማ የውሳኔ አሰጣጥ ችግር ወደ ግብነት ያልተቀየሩ ዕድሎችም በርካታ ናቸው። ከነዚህም ጁንያስ ናንጂቡ የተክለማርያም ሻንቆ ስህተት አግኝቶ ያመከነው ግልፅ የማግባት አጋጣሚ እና ገናናው ረጋሳ ከማዕዘን የተሻማውን ኳስ በግንባሩ ገጭቶ የግቡ አግዳሚ የመለሰበት ሙከራዎች ይጠቀሳሉ። ከተጠቀሱት ሙከራዎች ውጭም አሞስ አቼምፖንግ ከርቀት ያደረገው እና ጁንያስ ናንጂቡ ብሩክ ሰሙ ያሾለከለትን ኳስ ግብ ጠባቂው አታሎ ወደ ግብነት ያልቀየረው ሙከራ ይጠቀሳሉ።

የወልዋሎ ተደጋጋሚ ጥረት በመጨረሻም ፍሬ አፍርቶ 80ኛው ደቂቃ ላይ ጎል አስቆጥረዋል። ምስጋናው ወልደዮሐንስ ከማዕዘን ተሻምታ ተጨዋቾች የመለሷትን ኳስ በግርግር መሀል አግኝቶ በመምታት አስቆጥሮ ቡድኑን አቻ ማድረግ ችሏል። ጨዋታውም ተጨማሪ ጎል ሳይቆጠርበት በአቻ ውጤት ተገባዷል።

ውጤቱን ተከትሎ ወልዋሎዎች በ15 ነጥቦች አምስተኛ ደረጃን ሲይዙ ቡናዎች በ13 ነጥቦች ስምንተኛ ደረጃን ይዘዋል።


© ሶከር ኢትዮጵያ