የአሰልጣኞች አስተያየት | ስሑል ሽረ 3 – 0 ሀዋሳ ከተማ

ስሑል ሽረ ሀዋሳ ከተማን ሶስት ለባዶ ካሸነፈ በኃላ የሁለቱም ቡድን አሰልጣኞች የሚከተለውን አስተያየት ሰጥተዋል።

👉 “የምንፈልገው ነገር አሳክተናል” ሳምሶን አየለ (ስሑል ሽረ)

ስለ ጨዋታው

ከመሪዎቹ ላለመራቅ በእጅጉ ሦስት ነጥብ ያስፈልገን ነበር። ተሸንፈን እንደመምጣታችን እና ቀጣይ ከሜዳ ውጭ ስለምንወጣም ይህን ጨዋታ ማሸነፍ ይገባን ነበር። የምንፈልገው ነገር አሳክተናል።

በጣር የሆነ ቡድን ይዘው እንደሚገቡ ገምተን ነበር። በመጀመርያው አጋማሽ የመጨረሻ ደቂቃዎች ብልጫ ወስደውብን ዕድሎችም ፈጥረው ነበር። ያንን ችግር ግን በሁለተኛው አጋማሽ ለማስተካከል ሞክረናል። ከዕረፍት በኃላ ሁለት ጎሎች አስቆጥረን አሸንፈናል። በአጠቃላይ ግን ጎል አከባቢ ምናባክናቸው ዕድሎች ዋጋ እያስከፈሉን ነው። በእነሱ ላይም እየሰራን ነው።

ባለፈው ሳምንት ስለተፈጠረው ነገር

አዎ የደሞዝ ጥያቄ ነበረኝ። ግን ትንሽ ከጉንፋን ጋር በተያያዘ ጉሮሮየን አሞኝም ነበር። ከደሞዝ ጋር የተያያዘው ግን በሰፊው ተነጋግረን በነገው ዕለት ገቢ ይሆናል በሚል ተስማምተናል።

ስለ መድሀኔ ብርሀኔ ጉዳይ

አዎ ትክክል ነው ከረጅም ግዜ በኃላ ነው መድሀኔ ተቀይሮ የገባው። በአጭር ግዜ ቡድናችን ስለተቀላቀለ ነው፤ በሱ ቦታ ያለው ዲዲዬ ለብሪ በቀይ ስለወጣ ዕድሉን ሰጥተነዋል። በቀጣይ እሱ ላይም ጠንክረን እንሰራለን።

👉 “የሜዳው ሁኔታ ተፅዕኖ አድርጎብናል” አዲሴ ካሣ (ሀዋሳ ከተማ)

ስለ ጨዋታው

በሁሉም መልኩ ጥሩ ነበር ማለት ይቻላል። ጨዋታው ሲጀመር አካባቢ ማጥቅት ውስጥ ገብተው ነበር ጥሩ ነበሩ። ከዛ በኃላ እኛ የተሻልን ነበርን። ጎል ሲገባብህ ትወጣለህ። የመጨረሻ ላል የገቡብን ጎሎች ጎል ለማግባት እና ነጥብ ለመያዝ የወሰነው በሰዓቱ በደምብ ተጠቅመውበታል። ከጎሉ መብዛት ያየፈጠረው ነገር ነው።

ስለ ቡድኑ የወጥነት ችግር

የአገራችን ኳስ እንዲ እየሆነ ነው ፤ አንዴ ታሸንፋለህ አንዴ ትሸነፋለህ። ከሜዳ ውጭ ትሸነፋለህ በሜዳህ ታሸንፋለህ እንዲ እየሆነ ነው። ሁሉም ቡድኖች እንዲ የወጥነት ችግር አለባቸው። በሜዳህ ስትጨወት ብዙ የምታገኘው ነገር አለ። እነሱም ይሄን ተጠቅመውበታል።

ስለ ተፈጠሩት ዕድሎች በአግባቡ አለመጠቀም

በመጀመርያ ያገኘናቸው ኳሶች በአግባቡ ብንጠቀም ውጤቱ ይቀየር ነበር። ሄኖክም ብሩክም ዕድል አግኝተው ነበር አልተጠቀምንም። እንደዚህ እየተደጋገመብን ነው። ሜዳውም ተፅዕኖ አድርጎብናል። እኛ የምንሰራው ሌላ አይነት ሳር ላይ ነው። ኳስ ስትገፋም ሌላ ነገር ስታደርግም እንደ ስፖንጅ ነው የሚይዘን፤ ተፅዕኖ ሳያደርግብን አይቀርም። የሜዳው ሁኔታ ተፅዕኖ አድርጎብናል።

©ሶከር ኢትዮጵያ