ወላይታ ድቻ ጊዜያዊ አሰልጣኙን በቋሚነት ሾመ

ወላይታ ድቻን በጊዜያዊነት ተረክቦ የውጤት መሻሻል ያሳየው አሰልጣኝ ደለለኝ ደቻሳ በቋሚ ውል ቡድኑን ተረክቧል፡፡
አሰልጣኝ ገብረክርስቶስ ቢራራን ቢቀጥርም ከውጤት ማጣት ጋር በተገናኘ ከቦታው በማንሳት በክለቡ ከወጣት ቡድን ዋና አሰልጣኝነት ጀምሮ እስከ ዋናው ቡድን ድረስ በረዳት አሰልጣኝነት የሰራው ደለለኝ ደቻሳን በጊዜያዊነት መሾሙ ይታወሳል። በዚህም አሰልጣኙ ባለፉት ስምንት የሊጉ ጨዋታዎች ላይ ወላይታ ድቻን እየመራ በሁለቱ ብቻ ሽንፈት ሲገጥመው ስድስቱን በማሸነፍ ከፍተኛ የውጤት መሻሻል ማሳየቱን የተመለከተው የክለቡ ቦርድ አሰልጣኙን ቋሚ ለማድረግ መወሰኑን መዘገባችን ይታወሳል። በዚህም መሠረት የክለቡ ቦርድ አሰልጣኙ በአንድ ዓመት ውል ቡድኑን እንዲያሰልጥን ቋሚ አድርጎ ቀጥሯል፡፡

ወላይታ ድቻ በሁለተኛው ዙር የውድድር ጉዞው ላይ ደካማ አቋም አሳይተዋል ያላቸውን ተጫዋቾች ከቀነሰ በኋላ ከነገ ጀምሮ ወደ ዝውውር ገበያው በመግባት አዳዲስ ተጫዋቾች ለማስፈረም በዝግጅት ላይ መሆኑን ሰምተናል፡፡

© ሶከር ኢትዮጵያ