ኢትዮጵያ ቡና በመጨረሻም ከአማካዩ ጋር ተለያየ

ባሳለፍነው ዓመት አጋማሽ ኢትዮጵያ ቡናን ተቀላቅሎ የነበረው ሄኖክ ካሳሁን ከክለቡ ጋር በስምምነት ተለያይቷል።

በደደቢት፣ አዳማ ከተማ ፣ ጅማ አባ ቡና፣ ኢትዮ ኤሌክትሪክ እንዲሁም ዐምና በስሑል ሽረ ከተጫወተ በኃላ ሽረን በመልቀቅ በዓመቱ አጋማሽ ነበር ኢትዮጵያ ቡናን መቀላቀል የቻለው። በሁለተኛው ዙር አመዛኙ ጨዋታዎች ላይም የመሰለፍ ዕድል አግኝቶ መጫወት ችሎ ነበር። ሆኖም አሰልጣኝ ካሳዬ አራጌ ቡድኑን በተረከበበት ወቅት ከቡድኑ ጋር ከማይቀጥሉ ተጫዋቾች መካከል አንዱ ቢሆንም ሄኖክ ኮንትራቴ ይከበርልኝ በማለት ባቀረበው ቅሬታ በተፈጠረው አለመግባባት ጉዳዩን ወደ ዲሲፕሊን ኮሚቴ መሄዱ ይታወሳል። በዚህም ምንም እንኳ ተጫዋቹ በቡድኑ ስብስብ ውስጥ ባይኖርም ሁለቱ ወገኖች በይፋ ሳይለያዩ ቆይተዋል።

በመጨረሻም በሁለቱ ወገን በተደረገ ስምምነት መሠረት የክሱ ሒደት ተቋርጦ መለያየታቸው ታውቋል።

© ሶከር ኢትዮጵያ