የኤልያስ ማሞ ማረፍያ በቅርቡ ይታወቃል

ከብርቱካናማዎቹ ጋር ያለውን ውል ያጠናቀቀው አማካዩ ኤልያስ ማሞ ቀጣይ ማረፍያ በቀጣይ ቀናት ይታወቃል።

ባለፈው ዓመት በዚህ ወቅት ድሬዳዋ ከተማን የተቀላቀለው ኤልያስ ከክለቡ ጋር ያለው ውል መጠናቀቁን ተከትሎ ከቡድኑ ጋር ለመቀጠል ውሉን ያራዝማል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረ ቢሆንም ከቡድኑ ጋር ልምምድ አለመጀመሩን ተከትሎ ከክለቡ ጋር የመቀጠሉ ጉዳይ እርግጥ አልሆነም። ከሌሎች የፕሪምየር ሊጉ ክለቦችም ጋር ስሙ እየተነሳ የሚገኘው ይህ የቀድሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ፣ ጅማ አባጅፋር እና የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አማካይ ከብርቱካናማዎቹ ጋር ውሉን ያራዝማል ወይስ ወደ ሌሎች ክለቦች ይዘዋወራል የሚለው ጉዳይ በቀጣይ ቀናት ይለይለታል።

በውድድር ዓመቱ በአስራ አምስቱንም የሊግ ጨዋታዎች ቡድኑን በቋሚነት ያገለገለው እና በሁለት ጨዋታዎች ብቻ ተቀይሮ የወጣው ኤልያስ ማሞ በሊጉ አንድ ግብ ሲያስቆጥር ለሁለት ግቦች አመቻችቶ አቀብሏል።

©ሶከር ኢትዮጵያ