አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ እና ስሑል ሽረ ተለያይተዋል

ባለፈው ሳምንት የመልቀቂያ ደብዳቤ ያስገቡት አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ ከስሑል ሽረ ጋር በስምምነት ተለያይተዋል።

የመልቀቂያ ደብዳቤ ካስገቡ በኋላ ክለቡ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት ወደ ሽረ አቅንተው ከቡድኑ ጋር ሲወያዩ የቆዩ ሲሆን ክለቡ አሰልጣኙን ለማቆየት ጥረት ቢያደርግም በግል ጉዳይ ምክንያት መቀጠል እንደማይችሉ በመግለፅ በመጨረሻም ከአንድ ዓመት ቆይታ በኋላ መለያየታቸው እርግጥ ሆኗል። ክለቡም አዲስ አሰልጣኝ ለመሾም ከነገ ጀምሮ እንቅስቃሴ እንደሚያደርግ ሰምተናል።

ባለፈው ዓመት አጋማሽ ክለቡን ማሰልጠን የጀመሩት አሰልጣኙ ክለቡን ከማውረድ ማትረፋቸው ይታወሳል። በዚህ የውድድር ዓመትም ክለቡ ከቀዝቃዛ አጀማመር በኋላ መሻሻሎች አሳይቶ በ21 ነጥቦች የመጀመርያው አጋማሽን እንዲያጠናቅቅ የረዱት አሰልጣኙ በቀጣይ ቀናት ቀጣይ ማረፍያቸው ይታወቃል።

© ሶከር ኢትዮጵያ