ሀዲያ ሆሳዕና ሦስት ተጫዋቾችን ለማስፈረም ተስማማ

በዝውውሩ የነቃ ተሳትፎን እያደረገ የሚገኘው ሀዲያ ሆሳዕና ምኞት ደበበ፣ አበበ ጥላሁን እና አማኑኤል ጎበናን በማስፈረም ተስማማ፡፡

የቀድሞው የአርባምንጭ ከተማ እና ሲዳማ ቡና የመሐል ተከላካይ አበበ ጥላሁን ባለፉት ሁለት ዓመታት በመከላከያ በመጫወት አሳልፏል፡፡ ከፋሲል ከነማ ጋር ስሙ በስፋት ሲያያዝ የነበረው ይህ ተከላካይ ሆሳዕናን በአንድ ዓመት ውል ከደቂቃዎች በፊት ተቀላቅሏል፡፡

ሌላኛው ወደ ነብሮቹ ያመራው አማኑኤል ጎበና ነው፡፡ የቀድሞው የአርባምንጭ ከተማ የተከላካይ አማካይ ስፍራ ተጫዋች አርባምንጭ ከለቀቀ በኃላ በ2011 ወደ ወልዋሎ አምርቶ በመጫወት አሳልፏል፡፡ በተሰረዘው የዘንድሮው የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ደግሞ በአዳማ ከተማ ሲጫወት ካሳለፈ በኃላ አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለን ተከትሎ በአንድ ዓመት ውል ሀድያ ሆሳዕናን ተቀላቅሏል፡፡

የአሰልጣኝ አሸናፊ በቀለን ወደ ሀድያ ሆሳዕና መሄድ ተከትሎ ከቀድሞው ክለባቸው አዳማ በርከት ያሉ ተጫዋቾችን እያመሩ ሲሆን ምኞት ደበበም ስምንተኛው የሀዲያ ሆሳዕና ፈራሚ መሆኑ ዕርግጥ ሆኗል፡፡ ከደደቢት ወደ አዳማ ከተማ ካመራ በኋላ ድንቅ ዓመታትን ያሳለፈው ግዙፉ ተከላካይ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ስሙ ሲያያዝ ቢቆይም ወደ ሀዲያ ሆሳዕና ለማምራት ተስማምቷል፡፡

👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!


© ሶከር ኢትዮጵያ