መስፍን ታፈሰ የውጪ ዕድል አግኝቷል

በቅርብ ጊዜያት በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ከታዩ ተስፈኛ ወጣት ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው መስፈን ታፈሰ ከደቂቃዎች በፊት ወደ ኢኳቶሪያል ጊኒ በሯል።

ከሃዋሳ ከተማ የ17 እና 20 ዓመት በታች ቡድን ተነስቶ ወደ ዋናው የትውልድ ከተማው ክለብ ያደገው ተጫዋቹ በአጭር ጊዜያት የብዙዎች ዐይን ውስጥ መግባት ችሏል። ከክለብ በተጨማሪም በእድሜ እርከን ብሄራዊ ቡድኖች እና በዋናው የዋሊያዎቹ ስብስብ ውስጥ በመካተት ሃገሩን አገልግሏል። እያሳየ ያለውን ተስፋ ሰጪ አቋምን ተከትሎም ተጫዋቹ የውጪ ዕድል አግኝቶ ለሙከራ ወደ ኢኳቶሪያል ጊኒ ከደቂቃዎች በፊት አምርቷል።

የተጫዋቹ ህጋዊ ወኪል ሳምሶን ናስሮ ለሶከር ኢትዮጵያ እንደገለፁት ከሆነ ተጫዋቹን ለማስፈረም የግብዣ ደብዳቤ የላከው ክለብ የኢኳቶሪያል ጊኒው ፉቱሮ ኪንግስ ነው።

“ተጫዋቹን ለማስፈረም የፈለገው ክለብ ፉቱሮ ኪንግስ ነው። አሁን ወደ ኢኳቶሪየል ጊኒ እያመራን ነው። እዛም ተጫዋቹ ለ5 ቀናት ልምምድ እንዲሰራ ከተደረገ በኋላ የዛሬ ሳምንት ወደ ካሜሩን እንዲበር ይደረጋል። ካሜሩን የወዳጅነት ጨዋታ ላይ ብቃቱ ከታየ በኋላ ድጋሚ ቡድኑ ከቲፒ ማዜምቤ ጋር ላለበት የወዳጅነት ጨዋታ እንዲዘጋጅ ይሆናል። በጨዋታው ላይም ተሰልፎ ከታየ በኋላ ወሳኔዎች ይወሰናሉ።”

አቶ ሳምሶን ጨምረውም የፉቱሮ ኪንግ ዋና አሠልጣኝ ተጫዋቹን የማያምኑበት ከሆነ ከክለቡ ጋር የእህትማማችነት ግንኙነት ወዳላቸው የስፔን እና ግሪክ ክለቦች እንዲሄድ እና ተጨማሪ የሙከራ ጊዜ እንዲያገኝ ይደረጋል ብለዋል።

ፉቱሮ ኪንግ የተባለው የኢኳቶሪያል ጊኒው ክለብ ከመቐለ 70 እንደርታ ጋር ድንቅ ጊዜ ያሳለፈውን የግብ ዘብ ፍሊፕ ኦቮኖን ከሳምንታት በፊት በይፋ ማስፈረሙ ይታወሳል።

🌼🌻🌼🌻🌼🌻🌼🌻🌼🌻🌼🌻🌼🌻

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!