ባህር ዳር ከተማ የቅድመ ውድድር ዝግጅቱን የሚጀምርበት ቀን ታውቋል

በአሠልጣኝ ፋሲል ተካልኝ የሚመሩት የጣና ሞገዶቹ የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን የሚጀምሩበት ቀን አስታውቀዋል።

የአሠልጣኛቸውን ውል ካራዘሙ በኋላ ፊታቸውን ወደ ዝውውሩ በማዞር ራሳቸውን ሲያጠናክሩ የከረሙት ባህር ዳር ከተማዎች የቅድመ ውድድር ዝግጅታቸውን የሚጀምሩበትን ቀን ዛሬ ስለመወሰናቸው ተሰምቷል። በዚህም ክለቡ አዲስ ወደ ስብስቡ የቀላቀላቸውን አምስት ተጫዋቾች ጨምሮ ውል ያራዘሙትን ነባር ተጫዋች ከሐሙስ ጀምሮ ወደ ማረፊያቸው እንዲገቡ ተወስኗል።

ሐሙስ ጥቅምት 5 ቀን ተጫዋቾቹ እና የአሠልጣኝ ቡድን አባላቶቹ ባህር ዳር እንዲገቡ ከተደረገ በኋላ በቅድሚያ የኮቪድ-19 ምርመራ እንደሚደረግላቸው ለማወቅ ተችሏል። የምርመራው ውጤት ምናልባት እስከ ሰኞ ከደረሰ በኋላም ከቫይረሱ ነፃ የሆኑትን ተጫዋቾች በዓባይ ምንጭ ሎጅ በማሳረፍ መደበኛ የቅድመ ውድድር ዝግጅቱን በባህር ዳር ዓለማቀፍ ስታዲየም እንደሚከውን ሶከር ኢትዮጵያ ያገኘው መረጃ ይጠቁማል።

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!