ፋሲል ከነማ ዝግጅት ሊጀምር ነው

ፋሲል ከነማ የ2013 የውድድር ዓመት ቅድመ ዝግጅትን ለመጀመር ለተጫዋቾቹ ጥሪ አድርጓል።

በዝውውር መስኮቱ ላይ ጥሩ የሚባሉ ዝውውሮችን ያደረጉት እና ውል በማደሱ ላይ ስኬታማ ስኬታማ ሥራ ያደረጉት ፋሲሎች ከበርካታ ስብሰባ እና የውሳኔ መለዋወጥ በኋላ የካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ተሳታፊ እንዲሆኑ መወሰኑን ተከትሎ በኅዳር ወር መጀመርያ ለሚደረጉት የቅድመ ማጣርያ ጨዋታዎች እና መቼ እንደሚጀመር ላልታወቀው ፕሪምየር ሊግ ቅድመ ዝግጅት ለመጀመር እንቅስቃሴ እያደረጉ ይገኛሉ።

ዐፄዎቹ መስከረም 26 ወደ ጎንደር እንዲመጡ እና በሄርፋዚ ሆቴል እንዲያርፉ ለተጫዋቾቹ ጥሪ ያደረጉ ሲሆን በቀጣይ ቀናት የኮቪድ-19 እና አጠቃላይ ህክምና ምርመራ የሚያደርጉ ይሆናል። የሁሉም አባላት የምርመራ ውጤት በፍጥነት ላይሰበሰብ ስለሚችል በትክክል መቼ ልምምድ እንደሚጀምሩ ባይወሰንም እስከ ሳምንቱ መጨረሻ ወደ ቅድመ ዝግጅት ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል። ዘጠኝ ተጫዋቾችን ለብሔራዊ ቡድን ያስመረጡ በመሆኑ በቀሩት ተጫዋቾቻቸው ወደ ዝግጅት የሚገቡት ፋሲሎች የቅድመ ዝግጅት ውድድር ጊዜያቸውን በጎንደር የመጀመር እድላቸው ሰፊ ሲሆን ተጫዋቾቻቸውን ከብሔራዊ ቡድን መልስ ሲያገኙ የቦታ ለውጥ ሊያደርጉ እንደሚችሉ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!