ምዓም አናብስት ጋናዊውን ግብ ጠባቂ ለማስፈረም ተስማሙ

ባለፉት ሦስት የውድድር ዓመታት በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ከታዩ ጥሩ የውጭ ግብ ጠባቂዎች አንዱ የሆነው ጋናዊው ዳንኤል አጃይ ወደ መቐለ 70 እንደርታ ለማምራት ከስምምነት ደርሷል።

በ2009 ከጋና ጋር የዓለም ወጣቶች ቻምፒዮን የሆነው አጃይ ሲምባን ለቆ ጅማ አባ ጅፋርን ከተቀላቀለ በኃላ በመጀመርያ ዓመት የክለቡ ቆይታው ቡድኑ የሊጉን ዋንጫ እንዲያነሳ ድርሻ ከነበራቸው ተጫዋቾች አንዱ የነበረ ሲሆን የዓመቱ ምርጥ ግብ ጠባቂ ተብሎም ተመርጧል። በመቀጠል በተሰረዘው የውድድር ዓመት ወደ ሰበታ ከተማ አምርቶ ቆይታ ያረገው አጃይ አሁን ደግሞ መቐለን ለመቀላቀል ተስማምቷል። 

ከሁለት ቀናት በኃላ ወደ ኢትዮጵያ ገብቶ ከመቐለ ጋር እንደሚፈራረም የሚጠበቀው ይህ ጋናዊ በጅማ ካሰለጠኑት ገብረመድኅን ኃይሌ እና ዛሬ ከፈረመው አዳማ ሲሶኮ ጋር በድጋሚ የሚገናኝ ይሆናል። ወደ ሀገሩ የተመለሰው ወሳኙ ግብ ጠባቂያቸው ፊሊፕ ኦቮኖን ላጡት መቐለዎችም ጥሩ ፊርማ እንደሚሆን ይጠበቃል።

አጃይ ከዚህ ቀደም በሲምባ፣ ሊበሪቲ ፕሮፌሽናልስ፣ ፍሪ ስቴት ስታርስ እና መዳማ፣ በጋና ዋናው እና ከሀያ ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን መጫወት ችሏል።

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉ሳንዘናጋ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!